የከርሰ ምድር ውኃን በመጠቀም በበጋ ስንዴ መስኖ ውጤታማ ለመሆን እየሰራን ነው - ኢዜአ አማርኛ
የከርሰ ምድር ውኃን በመጠቀም በበጋ ስንዴ መስኖ ውጤታማ ለመሆን እየሰራን ነው
ሮቤ፣ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፡- በባሌ ዞን የከርሰ ምድር ውኃን በራሳቸው አቅም በማውጣት በበጋ ስንዴ መስኖ ልማት ውጤታማ ለመሆን እየሰሩ መሆናቸውን የአጋርፋ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ።
የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ በበኩሉ በአርሶ አደሩ እየተከናወኑ የሚገኙ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ኢኒሼቲቮችን ይበልጥ ውጤታማ የሚያደርግና የሚያዘምን የምርምር ፕሮጀክት እየተገበረ መሆኑ ተመልክቷል።
በዞኑ የአጋርፋ ወረዳ አርሶ አደሮች እንደሚሉት ዩኒቨርሲቲው በምርጥ ዘር አቅርቦት ድጋፍና በፍትሃዊ የውኃ አጠቃቀም ላይ ሙያዊ ድጋፍ እያደረገላቸው መሆኑን አመልክተዋል።
በልማቱ እየተሳተፉ ካሉ የወረዳው አርሶ አደሮች መካከል አቶ ሐሰን አህመድ በሰጡት አስተያየት፣ ከዚህ በፊት የዝናብ ውኃን ብቻ በመጠበቅ ስንዴና ሌሎች የግብርና ልማቶችን ያካሂዱ እንደነበር ተናግረዋል።
ካለፉት አራት ዓመታት ወዲህ ከዝናብ ውኃ በተጨማሪ በአካባቢያቸው የሚገኘውን የከርሰ ምድር ውኃን በራሳቸው አቅም በማውጣትና በመጠቀም ስንዴን በማልማት ይበልጥ ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን አመልክተዋል።
አርሶ አደር ሐሰን እንዳሉት ዩኒቨርሲቲው በፍትሃዊና ዘመናዊ የመስኖ ውኃ አጠቃቀም ላይ በተግባር የተደገፈ እገዛ እያደረገላቸው በመሆኑ ከአንድ ሄክታር እስከ 55 ኩንታል ስንዴ እንደሚጠብቁ አመልክተዋል።
ዩኒቨርሲቲው በምርጥ ዘር አቅርቦትና በመስኖ ዘርፍ የሚያጋጥሙንን ችግሮች እንዲፈቱልን እየደገፈን ስለሆነ የተሻለ ምርት ለማግኘት ተግተን እየሰራን ነው ያሉት ደግሞ ሌላው የወረዳው አርሶ አደር ሁሴን መሐመድ ናቸው።
አቶ ሁሴን እንዳሉት ዩኒቨርሲቲው በባለሙያ ምክርና እገዛ የተለያዩ የውሃ አማራጮችን በቁጠባ እንዲጠቀሙ እንዳገዛቸው ገልጸው፤ በማሳቸው ላይ የተለያዩ የስንዴ ዝርያዎችንም በማላመድ ለአካባቢው ተስማሚ የሆኑትን እንዲመርጡ ድጋፍ እያደረገላቸው መሆኑን ነው የገለጹት።
በዩኒቨርሲቲው የስንዴ ምርምር ፕሮጀክት ዋና አስተባባሪና ተመራማሪ ጀማል አብዱልከሪም (ረዳት ፕሮፌሰር) በበኩላቸው እንደገለጹት፣ ዩኒቨርሲቲው በአርሶ አደሩ እየተከናወኑ የሚገኙ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ኢኒሼቲቮችን ይበልጥ ውጤታማ የሚያደርግና የሚያዘምን የምርምር ፕሮጀክት እየተገበረ ነው።
ምርምሩ በዋናነት ቴክኖሎጂን በመጠቀም ለበጋ ስንዴ ልማት የሚያስፈልገውን የውኃ መጠንና የጊዜ ሰሌዳ ይወስናል ብለዋል።
“ይህንን ቴክኖሎጂ በመጠቀም የተለያዩ የስንዴ ዝርያዎችን በቦይ መስኖ እና በርጭት መስኖ ዘዴዎች መካከል የሚታዩ ልዩነቶችን አርሶ አደሩ እንዲረዳ በማሳው ላይ በተግባር እየፈተሽን እንገኛለን” ብለዋል።
አርሶ አደሩ በአየር ንብረት ለውጥ የማይበገሩና ከፍተኛ ምርት የሚሰጡ ዝርያዎችን ራሱ መርጦ እንዲያመርት ለማድረግ ያለሙ የተለያዩ ዝርያዎች ብዜቶች እየተካሄዱ መሆኑንም አክለዋል።
የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ብርሃነመስቀል ጠና (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ዩኒቨርሲቲው የአካባቢውን ማህበረሰብ ችግርና ፍላጎት መሰረት ያደረጉ የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።
የዩኒቨርሲቲው ተመራማሪዎች በስንዴ ምርምር ላይ በባሌና ምዕራብ አርሲ ዞኖች እያደረጓቸው የሚገኙት የቴክኖሎጂ ሽግግር ተግባራትም የዚሁ ማህበረሰብን የመለወጥ ትልቅ ጥረት አካል መሆናቸውን ፕሬዚዳንቱ አረጋግጠዋል።
ይህ የምርምር ፕሮጀክት በመስኖ ውኃ አጠቃቀም መስክ የሚስተዋሉ ችግሮችን በመፍታት፣ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ በዘርፉ የተሰማሩ አርሶና አርብቶ አደሮች ተጠቃሚነትን ይበልጥ ለማጉላት ዓላማ ማድረጉን አመልክተዋል።
የምርምር ፕሮጀክቱ የአሜሪካው ‘Grow Further’ ከተባለ ድርጅት ጋር በመቀናጀት በመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ እየተሰራ ያለ ሲሆን፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረውን የበጋ መስኖ ስንዴ ምርት ማነቆዎችን ለመፍታት ያለመ መሆኑ ገልጸዋል።
በባሌ ዞን በአሁኑ ወቅት ከ150 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ መሬት በበጋ መስኖ እየለማ መሆኑ ተገልጿል።