ቀጥታ፡

በክልሉ በልማታዊ ሴፍትኔትና ምግብ ዋስትና የታቀፉ ወገኖች ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ ነው

ባህር ዳር ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ከ231 ሺህ በላይ ወገኖች በከተማ ሴፍትኔትና ምግብ ዋስትና ፕሮግራም ታቅፈው  ሃብት በማፍራት ላይ መሆናቸውን የክልሉ ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ገለፀ።

የቢሮ ኃላፊው ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ በከተሞች የምግብ ዋስትናን በዘላቂነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ በርካታ ተግባራት በትብብር እየተከናወኑ ይገኛል።

በዚህም ከ195 ሺህ በላይ አነስተኛ ገቢ ያላቸውን ወገኖች በከተሞች በሚከናወኑ የልማት ስራዎች በማሳተፍ የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥም ባለፈ በዘላቂነት ሃብት እንዲያፈሩ እየተደረገ ይገኛል።

ተጠቃሚዎቹ በ18 ከተሞች በአረንጓዴ  እና በተፋሰስ ልማት፣ በከተማ ፅዳትና ውበት፣ በማህበራዊ ተቋማት ግንባታና መሰል የልማት ስራዎች እንዲሳተፉ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

ተጠቃሚዎቹ በተሰማሩበት መስክ በየወሩ ከሚያገኙት ክፍያ በተጨማሪም ከፕሮግራሙ ሲመረቁ በዘላቂነት በገቢ ማስገኛ ስራዎች እንዲሳተፉ እየተደረገ ነው ።

በተለይም በሰብል ልማት፣ በቁም እንስሳት ማድለብ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በጨርቃጨርቅና አልባሳት፣ በቆዳ ውጤቶች ስራና መሰል ዘርፎች እንዲሳተፉ በማድረግ ሃብት እንዲያፈሩ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።

በተጨማሪም ከ36 ሺህ በላይ አቅመ ደካሞች፣ የጤና ችግር ያለባቸውና ደጋፊ የሌላቸው ወገኖች በቀጥታ ድጋፍ ተጠቃሚ እየተደረጉ መሆኑን ገልፀዋል።

በተያዘው ዓመትም በፕሮግራሙ ታቅፈው ድጋፍ ሲደረግላቸው የቆዩና ተጨባጭ ለውጥ ያስመዘገቡ 18 ሺህ ተጠቃሚዎች ከፕሮግራሙ መመረቃቸውን አረጋግጠዋል።

ፕሮግራሙ የበርካታ ወገኖችን ኑሮ ከማሻሻሉም በላይ በከተሞች የሚከናወነውን ልማት እንዲፋጠን የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሆነም አብራርተዋል።

የፕሮግራሙ ውጤታማነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን ጠቅሰው፤ ቀጣይም የበለጠ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።

ለፕሮግራሙ ማስፈፀሚያ ከ3 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት ተይዞለት እየተተገበረ ሲሆን  39 ሺህ ወገኖች ከፕሮግራሙ ማስመረቅ እንደተቻለ ሃላፊው ጨምረው አስታውቀዋል።

በባህር ዳር ከተማ በፕሮግራሙ ታቅፈው ተጠቃሚ የሆኑት ወይዘሮ አስናቀች ደምለው እንዳሉት፤በፕሮግራሙ ተሳታፊ በመሆን በጀመሩት ቁጠባና የመቋቋሚያ ገንዘብ አሁን ላይ በሸቀጣሸቀጥ ንግድ ተሰማርተው እየሰሩ ይገኛል።

ቀደም ሲል ኑሯቸው ከእጅ ወደ አፍ እንደነበረ አስታውሰው፤ አሁን ላይ በሚያገኙት ገቢ ቤተሰባቸውን በአግባቡ ከማስተዳደር ባለፈ ሃብት በማፍራት ላይ መሆናቸውን ገልፀዋል።

በፕሮግራሙ ለሦስት ዓመታት በልማት ስራ ሲሳተፉ የቆየቱ ወይዘሮ ኤልሳ አሻግሬ ባስመዘገቡት ውጤት ተመርቀው በራሳቸው የንግድ ስራ ላይ መሰማራታቸውን ይገልፃሉ፡፡ 

አሁኑ ወቅትም በተደረገላቸው ሁሉን አቀፍ ድጋፍ ሃብት ለማፍራት መቻላቸውን ተናግረዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም