የሀዋሳ ከተማን ፈጣን እድገት የሚያሳልጡ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ኢዜአ አማርኛ
የሀዋሳ ከተማን ፈጣን እድገት የሚያሳልጡ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
ሀዋሳ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፡- የሀዋሳ ከተማን ፈጣን እድገት የሚያሳልጡ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ፡፡
ለሃዋሳ ከተማ ዘመናዊ የፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ፕሮጀክት ግንባታ የማስጀመሪያ መርሃ ግብር ተካሄዷል፡፡
ፕሮጀክቱን ያስጀመሩት የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞና የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞ (ዶ/ር) ናቸው፡፡
ርዕሰ መስተዳድሩ በወቅቱ እንደገለጹት፤ የሃዋሳ ከተማን እድገት የሚያሳልጡ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ፡፡
የዚሁ አካል የሆነው የሃዋሳ ከተማ ዘመናዊ የፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ግንባታ ከተማዋን ጽዱ በማድረግ የቱሪዝምና የኢንቨስመንት ማዕከልነቷን እንደሚያሳድገው አመልክተዋል።
የፕሮጀክቱ ግንባታ መንግስት ለከተሞች እድገት የሰጠውን ልዩ ትኩረት እንደሚያሳይ የጠቀሱት ርዕሰ መስተዳድሩ ግንባታው በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል፡፡
የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞ (ዶ/ር) በበኩላቸው በሀገሪቱ እየታየ ያለውን ፈጣን የከተሞች እድገት የሚመጥን የፍሳሽ ቆሻሻ አስተዳደር ስርዓትና የውሃ አቅርቦትን ለማሻሻል በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል፡፡
በዚህም ከአለም ባንክ በተገኘ ከ775 ሚሊዮን ዶላር በላይ ድጋፍ አዲስ አበባን ጨምሮ በ23 የሀገሪቱ ከተሞች 2ኛው የከተማ የውሃ አቅርቦትና የፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ፕሮጀክት ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ይህም 3 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዜጎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ገልጸው ሁለት ቢሊዮን ብር በሚጠጋ ወጪ የሚገነባው የሃዋሳ ዘመናዊ ፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ፕሮጀክትም የዚሁ አካል ሆኖ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል ብለዋል፡፡
ፕሮጀክቱ የአካባቢ ጥበቃና ዘላቂ የፍሳሽ ቆሻሻ አወጋገድ ስርዓትን ከማጠናከር ባለፈ ፍሳሹን ለመልሶ ማልማት ስራ በማዋል ለአካባቢው ማህበረሰብ የስራ እድል ይፈጥራል ያሉት ደግሞ የክልሉ ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ሃላፊ ኢንጂነር ከበደ ጋኖሌ ናቸው፡፡
ይህም በፈጣን እድገት ላይ ለምትገኘው ሃዋሳ ከተማ አለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን እንደሚጨምር ገልጸዋል፡፡
የሃዋሳ ከተማ ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ አገና ኔቶ በበኩላቸው ዘመናዊ የፍሳሽ ማጣሪያ ፕሮጀክቱ የሃዋሳ ከተማን ፈጣን እድገት ታሳቢ ያደረገና ሃይቋን ከብክለት የሚከላከል ነው ብለዋል፡፡