ማዕከሉ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያግዙ የተሻሻሉ የሰብል ዝርያዎችን ተደራሽ እያደረገ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ማዕከሉ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያግዙ የተሻሻሉ የሰብል ዝርያዎችን ተደራሽ እያደረገ ነው
ሮቤ፤ ግንቦት 11/2018(ኢዜአ)፡- የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል የአርሶ አደርና አርብቶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚያግዙ የተሻሻሉ የሰብል ዝርያዎችን ተደራሽ እያደረገ መሆኑን አስታወቀ።
ማዕከሉ በምርምር ያገኛቸውን 12 የተሻሻሉ ዝርያዎች የለቀቀ ሲሆን፣ ዝርያዎቹ በሽታን የመቋቋም አቅማቸው ቀደም ሲል ከነበሩት የተሻሉ ከመሆናቸው ባሻገር፣ ከ14 እስከ 33 በመቶ የምርት ብልጫ ያላቸው እንደሆነም ተመላክቷል።
የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር አቶ ጌታቸው አሰፋ ለኢዜአ እንዳሉት፣ ማዕከሉ የአርሶ አደርና አርብቶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በምርምር እየደገፈ ነው።
በተለይም ማዕከሉ ባለፉት ዓመታት በስንዴ፣ በገብስና በሌሎች ስምንት የትኩረት መስኮች ላይ ምርምሮችን በማካሄድ 116 የምርምር ውጤቶችን ለተጠቃሚው ማድረሱን አስታውሰዋል።
በዘንድሮው የበጀት ዓመትም ባለፉት ስድስት ዓመታት በምርምር ሥር የነበሩ 12 የተሻሻሉ ዝርያዎችን ለተጠቃሚው መልቀቁን አመልክተዋል።
በምርምር የተለቀቁት ዝርያዎች 4 የቦሎቄ ዝርያዎች፣ 2 የማሾ፣ 2 የድንች ዝርያዎችን ጨምሮ ሌሎች የአተር፣ የማሾ፣ የቆሎ ገብስ፣ የምስርና የባቄላ ዝርያዎች እንደሚገኙበት ተናግረዋል።
አዳዲስ የተለቀቁት እነዚሁ ዝርያዎች በሽታን በመቋቋም አቅማቸው በፊት ከነበሩት ዝርያዎች የተሻሉ ከመሆናቸው ባሻገር፣ ከ14 እስከ 33 በመቶ የምርት ብልጫ ያላቸው እንደሆነም አመልክተዋል።
ዝርያዎቹ በብሔራዊ የዝርያ አጽዳቂ ኮሚቴ ከተገመገሙ በኋላ፣ ከሚያዝያ ወር 2018 ዓ.ም ጀምሮ ዕውቅና አግኝተው ለሕብረተሰቡ የተለቀቁ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በማዕከሉ የሰብል ምርምር የሥራ ሂደት አስተባባሪና ተመራማሪ አቶ ታደለ ታደሰ በበኩላቸው፣ ከተለቀቁት ዝርያዎች መካከል የቦሎቄ ዝርያዎቹ በሄክታር በአማካይ ከ19 እስከ 26 ኩንታል፣ እንዲሁም የድንች ዝርያዎቹ ከ500 እስከ 531 ኩንታል ምርት እንደሚሰጡ መረጋገጡን ተናግረዋል።
ዝርያዎቹ የተሻለ ምርት ከመስጠታቸው ባሻገር፣ ከነባር ዝርያዎች ጋር ሲነጻጸር ከ14 እስከ 33 በመቶ ጭማሪ እንዳላቸውም አመልክተዋል።
ዝርያዎቹ የባሌ ዞን ቆላና ወይናደጋን ጨምሮ ሌሎች ተመሳሳይ ሥነ-ምህዳር ባላቸው የሀገሪቱ አካባቢዎች ተስማሚ መሆናቸውንም ተመራማሪው አስረድተዋል።