ቀጥታ፡

ጉምሩክ ኮሚሽን አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድን በመከላከል ከፍተኛ ሚናውን እየተወጣ ነው

አዲስ አበባ፤ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ ጉምሩክ ኮሚሽን ህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድን መከላከል እና የገቢ አሰባሰብን የሚያዛቡ የተጭበረበሩ ሰነዶችን መቆጣጠር የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም በተቋም ግንባታ የፋና ወጊነት ሚና እየተወጣ መሆኑን የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡

የፌደራል መንግሥት አስፈፃሚ አካላትን ሥልጣንና ተግባር ለመወሰን በወጣው አዋጅ ቁጥር 1097/2011 መሰረት የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን እንዲቋቋም ተደርጓል፡፡

በዚህም ሀገራዊ ሪፎርሙን ተከትሎ ተቋማዊ ሪፎርም በማድረግ ህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድን መከላከል፣ የገቢ አሰባሰብን ማሳደግ የሚያስችል አደረጃጀት ፈጥሯል፡፡

የጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ተቋሙ በአዋጅ ከተሰጠው ቁልፍ ተልዕኮዎች መካከል ከገቢና ወጭ እቃዎች ታክስን አስልቶ ገቢ መሰብሰብ ነው፡፡

ሀገራዊ ሪፎርሙን ተከትሎ በተደረገው የተቋም አደረጃጀት ህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድን መከላከል የሚያስችሉ ግልጽ የህግ ማዕቀፎች ተዘጋጅተዋል ብለዋል፡፡

በኢትዮጵያ ከሪፎርሙ በፊት በ2011 በጀት ዓመት የተሰበሰበው ገቢ 78 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር እንደነበር ገልጸው፤ በተያዘው በጀት ዓመት አስር ወራት ከታቀደው በላይ 600 ነጥብ 23 ቢሊየን ብር በላይ ጥቅል ገቢ ተሰብስቧል ብለዋል፡፡

ሪፎርሙ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም፣ ህጎችን በማሻሻልና አሰራርን በማዘመን የገቢ አሰባሰብ፣ የህገ ወጥና ኮንትሮባንድን መከላከል የሚያስችል አቅም መፍጠሩን ገልጸዋል፡፡

ኮሚሽኑ ዕቃዎችን ከአደጋ በመከላከል ደህንነታቸው ተጠብቆ ከመዳረሻ ቦታቸው እንዲደርሱ የሚያስችል የኤሌክትሮኒክ ካርጎ ትራኪንግ ቴክኖሎጂ ሥራ ላይ አውሏል ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ ወደ ውጭ በምትልካቸው እቃዎች በመንገድ ላይ ይደርስ የነበረውን መዘግየት፣ ቅሸባና ስርቆት እና መሰል ችግሮች እንዳይከሰቱ መቆጣጠር የሚያስችል ቴክኖሎጂ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

በቴክኖሎጂ የታገዘ የተቀናጀ የድንበር ቁጥጥር ስርዓት በመዘርጋት የካርጎ እንቅስቃሴዎችን ማዕከል ላይ ሆኖ መቆጣጠር የሚቻልበት ዕድል ተፈጥሯል ብለዋል፡፡

ከዚህም ባለፈ የተገልጋይ መንገደኞችን እንቅስቃሴ በመቆጣጠር ህገ ወጥ እንቅስቃሴን መከላከልና መቆጣጠር የሚያስችል ቴክኖሎጂ ጥቅም ላይ መዋሉን ገልጸዋል፡፡

ኮሚሽኑ ሪፎርሙ በፈጠራቸው መልካም ዕድሎች ዘመናዊና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት በኢትዮጵያ የተቋማት ግንባታ ፋና ወጊ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በርካታ ቴክኖሎጂዎች ሥራ ላይ መዋላቸውን ገልጸው፤ የማንዋል አሰራርን በማስወገድ ለአምራቾች፣ አስመጭዎችና ላኪዎች የተሳለጠ አገልግሎት እየሰጡ ነው ብለዋል፡፡

የኦን ላይን አገልግሎቶችን በመስጠት የተገልጋዮችን ጊዜና ጉልበት ይቀንሳል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ቴክኖሎጂዎች ህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድ መከላከል እና የገቢ አሰባሰብን የሚያዛቡ የተጭበርበሩ ሰነዶችን መቆጣጠር እንዳስቻሉ ገልጸዋል፡፡

ይህም የማንዋል አሰራሮችን በማስቀረት ብልሹ አሰራርን በማስወገድ ኮሚሽኑ ተልዕኮውን በብቃት እንዲወጣ ማስቻሉን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም