ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ የባህር በር የማግኘት ጥያቄ ተገቢና ህጋዊ ነው - አምባሳደር አሌክሲ ላሜክ

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018(ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ የባህር በር ለማግኘት የምታደርገው ጥረት ፍጹም ህጋዊ መሆኑን በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲ ላሜክ ገለጹ።

አምባሳደሩ ይህ ጥያቄ በዓለም ላይ በብዛት ህዝብ ካላቸው ሀገራት ተርታ ለምትሰለፈው ኢትዮጵያ ተገቢና ምክንያታዊ መሆኑንም ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ተናግረዋል።

የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከአንድ ዓመት ተኩል ገደማ በፊት በኢትዮጵያ ባደረጉት ጉብኝት ወቅት የገለጹትን አቋም ያስታወሱት አምባሳደሩ፤ ጉዳዩ አሁንም ቢሆን መሰረታዊና ህጋዊ ጥያቄ ሆኖ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።

ኢትዮጵያ የባህር በር ለማግኘት መፈለጓ ፍጹም ህጋዊ ነው ያሉት አምባሳደሩ፤ ለዚህም የሀገሪቱን ሰፊ የህዝብ ቁጥርና ያላትን መልክዓ-ምድራዊ አቀማመጥ እንደ ዋነኛ ምክንያት ጠቅሰዋል።

በርካታ ታዛቢዎች እንደሚስማሙት፣ የቀይ ባህር ጉዳይ ከኢትዮጵያ ታሪካዊ ቅርስ፣ ከጥንታዊ ስልጣኔዋ፣ ከሀገረ መንግስት ምስረታዋ፣ ከብሄራዊ ደህንነትና ከረጅም ጊዜ የኢኮኖሚ ግቦች ጋር ጥብቅ ቁርኝት ያለው ነው።

ኢትዮጵያም ይህንን መልክዓ-ምድራዊ፣ ታሪካዊና ኢኮኖሚያዊ አውድ መሰረት በማድረግ፣ በጋራ ተጠቃሚነትና በአጋርነት መርህ ላይ የተመሰረተ የባህር በር ተደራሽነትን ለማረጋገጥ እንዲሁም ለጋራ ልማት የሚረዱ ውይይቶችን ስታካሂድ ቆይታለች።

ሀገሪቱ የባህር በር ባለቤትነትን በተመለከተ ያላትን ሉዓላዊ መብት ለማረጋገጥ፣ በትውልዶች መካከል የተሸጋገረውን ይህን ጥያቄ በዲፕሎማሲያዊና በህጋዊ መንገዶች መፍትሄ እንዲያገኙ እየሰራች ትገኛለች።

አምባሳደር አሌክሲ ፈረንሳይ የኢትዮጵያን የባህር በር ጥያቄ ለመፍታት የሚደረጉ ገንቢ ጥረቶችን ለመደገፍ ዝግጁ መሆኗን ጠቁመው፤ በዚህ ረገድ ፈረንሳይ የምታበረክተው ማንኛውም እገዛ ካለ ድጋፍ ለመስጠት ፍላጎቱ አለን ብለዋል።

ለዚህም የአውሮፓ ሀገራት ተሞክሮ ለቀጣናው ጠቃሚ ትምህርት ሊሰጥ እንደሚችል የጠቆሙት አምባሳደሩ፤ ጠንካራ ኢኮኖሚ ያላቸው በርካታ የአውሮፓ ወደብ አልባ ሀገራት ከጎረቤቶቻቸው ጋር በመተባበር አስተማማኝ የባህር በር ማግኘት መቻላቸውን ለአብነት አንስተዋል።

እንደ አምባሳደሩ ገለጻ፣ እነዚህ ሀገራት ወደብ ካላቸው ጎረቤት ሀገራት ጋር በመተማመን ላይ የተመሰረተ ግንኙነትን መገንባት መቻላቸው ለስኬታቸው ቁልፍ ሚና ተጫውቷል።

እንዲህ ዓይነቱን ግንኙነት ለመገንባት ጊዜ ቢወስድም፣ አካሄዱ ግን በጣም ውጤታማና የባህር በር አማራጮችን ለማግኘት ተመራጭ መንገድ መሆኑን አመልክተዋል።

አምባሳደሩ አክለውም፣ እንዲህ ዓይነቱ ትብብር ወደብ አልባ ከመሆን የሚመነጩና ሊካዱ የማይችሉ ማነቆዎችን ለመፍታት ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል።

ኢትዮጵያ ሁለንተናዊ የኢኮኖሚ እድገትና ቀጣናዊ ትስስርን ለማጠናከር፣ የባህር በር ለማግኘት የምታደርገውን ዲፕሎማሲያዊ ጥረት አጠናክራ ቀጥላለች።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም