ቀጥታ፡

አዋጁ የህብረት ስራ ማህበራት ለሀገር ኢኮኖሚ የሚያበረክቱትን አስተዋፅኦ የሚያሳድግ ነው

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፦ የህብረት ስራ ማህበራት ማሻሻያ አዋጅ የማህበራቱን ተወዳዳሪነትና ለሀገር ኢኮኖሚ የሚያበረክቱትን አስተዋፅኦ የሚያሳድግ መሆኑን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ገለፀ።   

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው አምስተኛ ዓመት የስራ ዘመን 21ኛ መደበኛ ስብሰባ የህብረት ስራ ማህበራት ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅን መርምሮ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል።


 

የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ፤ የማሻሻያ ረቂቅ አዋጁን አስመልክቶ ባቀረቡት ሪፖርትና የውሳኔ ሐሳብ በረቂቅ አዋጁ ዙሪያ በርካታ የባለድርሻ አካላትና የአስረጂ መድረክ መካሄዱን አንስተዋል።

ነባሩ አዋጅ 985/2009 ከሀገሪቱ አሁናዊ ነባራዊና የሪፎርም ሂደት ጋር ያልተጣጣመ ነው ብለዋል።

የህብረት ስራ ማህበራት ጠንካራ የውስጥ አመራርና የአስተዳደር ስርዓት ያለመኖር እንዲሁም ዘመናዊ የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓት ያለመተግበር ችግር ይስተዋልባቸው እንደነበር አንስተዋል። 

የማሻሻያ አዋጁ የተበታተኑና ውጤታማ ያልሆኑ በርካታ የህብረት ስራ ማህበራት ሰብሰብ ብለው እንዲደራጁና ትርፋማ የሚሆኑበት አሰራር እንዲዘረጉ የሚያስችል ነው ብለዋል።

የህብረት ስራ ማህበራት ያለባቸውን የፋይናንስ አቅርቦት እጥረት በመፍታት ከፋይናንስ ተቋማት ጋር እንዲሁም የእርስ በርስ ትስስራቸውን የሚያጠናክር መሆኑንም ተናግረዋል።

ብልሹ አሰራርና ብክነትን ለማስተካከል የሚያስችል የቁጥጥርና ተጠያቂነት አሰራርን እንደሚያጠናክር ነው ያነሱት።

የህብረት ስራ ማህበራት ለሀገር ኢኮኖሚ ያላቸውን አስተዋፅኦ እንደሚያሳድግና የኦዲት ስርዓታቸውን እንደሚያጠናክር በማንሳት፥ ምክር ቤቱ የአዋጁን አስፈላጊነት በመገንዘብ እንዲያፀድቀው ጠይቀዋል።

የምክር ቤቱ አባላት አዋጁ አሳሪ አሰራሮችን የሚፈታና የህብረት ስራ ማህበራት ከፋይናንስ ተቋማት ጋር ያላቸውን ትስስር እንዲሁም የማህበራቱን እርስ በርስ ትብብር የሚያጠናክር መሆኑን ገልፀዋል።

በዚህም የህብረት ስራ ውስጥ በኢንቨስትመንት ለመሰማራት የሚፈልግ ግለሰብና ተቋም ድርሻ እንዲሁም በማህበራት አመራርነት ላይ ስለሚኖር አካታችነት ድርሻ የተመለከቱ ጥያቄዎች አቅርበዋል። 


 

የኢትዮጵያ ህብረት ስራ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሺሰማ ገብረ ሥላሴ፤ አዋጁ ሲዘጋጅ የሌሎች ሀገራት ተሞክሮን በመውሰድ የተዘጋጀ መሆኑን ተናግረዋል።

የኢንቨስትመንት ድርሻን በተመለከተ በሰጡት ምላሽ ማህበራትን የበለጠ ውጤታማ ለማድረግ ትብብርን ማጠናከር ወሳኝ በመሆኑ የተካተተ ነው ብለዋል።

የማህበራት አመራር አካታችነት ባሉት የአባላት ቁጥር እንደሚወሰንና የሴቶች፣ አካል ጉዳተኞችና ወጣቶች ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ ናቸው።

በዚህም መሰረት ምክር ቤቱ የቀረበውን ረቂቅ አዋጅ ቁጥር 1416/2018ን በሙሉ ድምፅ አፅድቋል። 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም