ቀጥታ፡

ኢትዮጵያ በልማት ዘርፎች የጀመረቻቸው ግዙፍ ተግባራት ቃል በተግባር የተፈጸመባቸው ድሎች ናቸው -የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 3/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በተለያዩ የልማት ዘርፎች የጀመረቻቸው ግዙፍ ተግባራት የትውልድ ተስፋ ከመሆን ባለፈ፣ በተጨባጭ ስኬቶች የታጀቡና ቃል በተግባር የተፈጸመባቸው ድሎች መሆናቸውን የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት አስታወቀ።

በግብርናው ዘርፍ፣ በተለይም በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት የታየው ዐቢይ ለውጥ ሀገሪቱን ከውጪ የዕርዳታ ስንዴ ጥገኝነት አላቆ ራስን ወደ መቻል ከፍ ማድረጉንም ገልጿል።

ምርቱን ለውጭ ገበያ ማቅረብ (ኤክስፖርት) መጀመሩም፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ትግል ወደ አዲስ ምዕራፍ ማሸጋገሩን ጠቁሟል።

በኢንዱስትሪው መስክ የውጭ ምንዛሬ ፍሰትን ለመታደግ የተወጠነው "የተኪ ምርቶች ንቅናቄ"፣ የኢንዱስትሪ ግብአቶችንና የፍጆታ ዕቃዎችን በሀገር ውስጥ በማምረት ረገድ ተስፋ ሰጭ ውጤቶችን እያስመዘገበ እንደሚገኝ አገልግሎቱ አመልክቷል።

ይህም ሀገራዊ ምርታማነትን በማነቃቃት የኢኮኖሚውን መዋቅር እያጠናከረ ስለመሆኑም አጽንኦት ሰጥቷል።

የከተሞችን ገጽታ ለማሻሻልና ለዜጎች ክብር ያለው ሕይወት ለመስጠት የተጀመረው የኮሪደር ልማት፣ አዲስ አበባንና የክልል ከተሞችን የኮንፈረንስ ቱሪዝም መዳረሻ ከማድረግ ባለፈ፣ ደረጃቸውን የጠበቁ መሠረተ ልማቶችን እውን በማድረግ ዜጎች በሀገራቸው አዲስ ተስፋ እንዲሰንቁ ማድረጉን አገልግሎቱ አውስቷል።

የኢትዮጵያዊያን የጋራ ትብብር ማሳያ በሆነው በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም ኢትዮጵያ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል፣ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በሚደረገው ዓለም አቀፍ ጥረት ቀዳሚ ከሆኑ አገራት ተርታ እንድትሰለፍ ያደረገ የማይደበዝዝ አሻራ ማኖሯን አስገንዝቧል።

ነባር የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማደስ፣ አዳዲስ መዳረሻዎችን በመገንባትና የንጹህ ኢነርጂ ኢንቨስትመንቶችን በማስፋፋት የተሰራው ወሳኝ ሥራ፣ ሀብቶች ለኢኮኖሚ መሰረት እንዲሆኑ በማስቻል ረገድ ፍሬው የሚታይበት ወሳኝ ጊዜ ላይ እንደሚገኝም አስታውቋል።


እነዚህ ስኬቶች የመንግሥትና የሕዝብ የጋራ ቁርጠኝነት ውጤቶች መሆናቸውን የጠቀሰው አገልግሎቱ፤ ኢትዮጵያ በትክክለኛ የልማትና የዕድገት ጎዳና ላይ መሆኗንና በዜጎች ሕይወት ላይ ተጨባጭ ለውጥ የሚመጣበት የታሪክ ምዕራፍ ላይ መደረሱን የሚያረጋገጥ እንደሆነ አገልግሎቱ በመረጃው አመልክቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም