በከተማ አስተዳደሩ ከ36 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደዋል - ኢዜአ አማርኛ
በከተማ አስተዳደሩ ከ36 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደዋል
ባህር ዳር ፤ግንቦት 3/2018 (ኢዜአ)፡-በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ከ36 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰጠቱን የከተማ አስተዳደሩ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ገለፀ።
በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የመምሪያው ኃላፊ ብርሃን ንጉሴ ለኢዜአ እንዳሉት፤በከተማዋ የኢንቨስትመንት ዘርፉን በተቀናጀ አግባብ ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ስኬታማ ናቸው ።
ባለፉት ዘጠኝ ወራትም 320 አዳዲስ ባለሃብቶች መዋለ ንዋያቸውን ለማፍሰስ የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደዋል ብለዋል።
ባለሃብቶቹ ከ36 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ሲሆን ወደ ስራ ሲገቡም ከ19 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የስራ እድል የመፍጠር አቅም እንዳላቸው ተናግረዋል።
ባለሃብቶቹ ፈጥነው ወደ ስራ እንዲገቡ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን አንስተው፤ በዚህ ዓመትም መስፈርቱን ለሚያሟሉ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች 102 ሄክታር መሬት መዘጋጀቱን ገልፀዋል።
በከተማው ቀደም ሲል የኢንቨስትመንት ቦታ ወስደው ተደጋጋሚ እገዛና ድጋፍ ተደርጎላቸው ወደ ስራ ያልገቡ 24 ባለሃብቶችም የወሰዱትን ቦታ እንዲመልሱ መደረጉንም አስታውቀዋል።
በከተማዋ በኮሪደር ልማት የተከናወኑት ተግባራት ለኢንቨስትመንት ይበልጥ ተመራጭ እንድትሆን ያደረጉ ሲሆን በተለይ በአገልግሎትና ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ መሰማራት ለሚፈልጉ ምቹ ሁኔታ እንዳለ አመልክተዋል።
ከተማ አስተዳደሩ ኢንቨስትመንትን ከማሳደግ ጎንለጎንም ባለፉት ዘጠኝ ወራት በተካሔደ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ 23 ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት እንዲገቡ ማድረጉን ገልፀዋል።
በዚህም ከ 3 ሺህ 800 ለሚበልጡ ወገኖች የስራ ዕድል መፍጠር መቻሉንም ገልፀዋል
በ98 ኢንዱስትሪዎችም 155 ነጥብ 6 ቶን ተኪ ምርት በማምረት ከ118 ነጥብ 7 ሚሊዮን በላይ ዶላር የውጭ ምንዛሬ ማዳን እንደተቻለ አስረድተዋል።
ዘጠኝ አምራች ኢንዱስትሪዎች 17 ነጥብ 7 ቶን የተለያዩ ምርቶችን ወደ ውጭ ሃገራት ገበያ በመላክ 22 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ተገኝቷል ነው ያሉት።
የኢትዮጰያ ታምርት ንቅናቄ የኢንዱስትሪዎችን የማምረት አቅምም ከ59 በመቶ ወደ 63 በመቶ ከፍ ማድረግ እንዳስቻለም አስገንዝበዋል።
በከተማ አስተዳደሩ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች የተሰማሩ 287 ኢንዱስትሪዎች እንዳሉም የመምሪያ ኃላፊዋ ጨምረው አስታውቀዋል።