ቀጥታ፡

የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ለሳፋሪኮም ኢትዮጵያ የአገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት መጠናከር ጉልህ አስተዋፅኦ እያበረከተ ይገኛል

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 3/2018(ኢዜአ)፦ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ለሳፋሪኮም ኢትዮጵያ የአገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት መጠናከር ጉልህ አስተዋፅኦ እያበረከተ እንደሚገኝ የኩባንያው ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዊም ቫንሄሌፑቴ ገለጹ።

ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ከመጋቢት 23 ቀን 2017 ዓ.ም እስከ መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ያለውን የሥራ አፈፃጸም አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫ ሰጥቷል።

መግለጫውን የሰጡት የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዊም ቫንሄሌፑቴ፤ ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ፈጣን ዕድገት እያስመዘገቡ ካሉ ሀገራት መካከል አንዷ ናት ብለዋል።

ለዚህም ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብሩ ዕድገትን በማፋጠን በኩል ከፍተኛ ሚና እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል።

በኢትዮጵያ ፈጣንና ጤናማ የኢኮኖሚ ዕድገት ውስጥ በኢንቨስትመንት መሳተፍ አስደሳች መሆኑን ጠቁመው፤ የማክሮ ኢኮኖሚ አመላካች አዎንታዊ ውጤቶች ኢንቨስትመንትን በማበረታታት ምቹ የልማት ምኅዳር መፍጠሩን ተናግረዋል።

በቴሌኮም ዘርፍም አበረታች የቁጥጥር ለውጦች መምጣታቸውን ገልጸው፤ ይህም የሳፋሪኮም ኢትዮጵያን የ90 ቀናት ንቁ ደንበኞች ቁጥር 13 ነጥብ 6 ሚሊየን ማድረስ ማስቻሉን አስረድተዋል።

ይህም ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ54 ነጥብ 2 በመቶ ዕድገት ማሳየቱን በመግለጽ።

የኤም-ፔሳ (M-PESA) ተጠቃሚዎች ቁጥር 5 ነጥብ 2 ሚሊየን መድረሱንና በመተግበሪያው የተደረገው የገንዘብ ዝውውርም 32 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር መድረሱን አብራርተዋል።

የሞባይል ዳታ አገልግሎት በዓመታዊ ገቢ ላይ ትልቁን ድርሻ በመያዝ ጠንካራ ዕድገት ማሳየቱንም ጨምረው ጠቁመዋል።

በተጠናቀቀው የ2026 በጀት ዓመት 15 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር ገቢ ማግኘቱንና ይህም የ130 ነጥብ 9 በመቶ ዕድገት እንዳለው አመላክተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም