የአፍሪካን ዓለምአቀፍ ትርክት በአዲስ መልክ ለመቅረጽ ያለመው ጉባኤ - ኢዜአ አማርኛ
የአፍሪካን ዓለምአቀፍ ትርክት በአዲስ መልክ ለመቅረጽ ያለመው ጉባኤ
በሙሴ መለሰ
የመጀመሪያው የማህበራዊ ሚዲያ ተጽእኖ ፈጣሪዎች ጉባኤ (ASMIS2026) በአፍሪካውያን መዲና አዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል።
ጉባኤው አፍሪካ በዓለም መድረክ ያላትን ስፍራ ዳግም ለመወሰን ለሚደረገው ጥረት ትልቅ አቅም ነው።
ይህ ታሪካዊ ጉባኤ ከባህላዊ ብዝሃነት ድምቀት ባለፈ፣ ስትራቴጂካዊ ውይይቶችና ለውጥ አምጪ ሃሳቦች የሚፈልቁበት ጠንካራ መድረክ ነው። የአህጉሪቱ የዲጂታል ይዘት ፈጣሪዎች እና ቁንጮ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች የተሰባሰቡበት ሲሆን የተስፋ፣ የፈጠራና የጽናት ትስስርን በመፍጠር የአፍሪካን ግዙፍ አቅም ለዓለም እያስተጋቡ ይገኛሉ።
የጉባኤው ተሳታፊዎች የትናንት ጉብኝት የአዲስ አበባን ጥልቅ ታሪክና ደማቅ ባህል በቅርበት እንዲገነዘቡ ዕድል ሰጥቷቸዋል። በቆይታቸውም የኢትዮጵያን የነፃነት ተምሳሌት የሆነውን የአድዋ ድል መታሰቢያን፣ የሀገሪቱ መለያ የሆነው እንጀራ የሚዘጋጅበትን የጉለሌ እንጀራ ማምረቻን እንዲሁም የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩትን ተመልክተዋል።
እነዚህ ጉብኝቶች በተሳታፊዎች መካከል መቀራረብንና ወንድማማችነትን ያጠናከሩ ሲሆን፣ ለቀጣይ ቁም ነገር አዘል ውይይቶችም ስንቅ ሆነዋል። ተጽዕኖ ፈጣሪዎቹ በከተማዋ ጎዳናዎች ላይ የሚያሳዩት ከፍተኛ ጉጉት፤ በእውነተኛነት፣ በብዝሃነትና በስልጣኔ ላይ ከተመሰረተው አዲሱ የአፍሪካ ትርክት ጋር ተሳስረው ልዩ ድባብ ፈጥረዋል።
ዛሬ ጉባኤው ከባህላዊ ትውውቅ ወደ ስትራቴጂካዊ ምክክር የተሸጋገረ ሲሆን፣ የተለያዩ ውይይቶች በአድዋ ድል መታሰቢያ ይካሄዳሉ።
ውይይቱ ትኩረቱን የዲጂታል ፈጠራን - በተለይም ሰው ሰራሽ አስተውሎትን (AI) በመጠቀም የአፍሪካን ድምጽ ለማጉላትና አሉታዊ አመለካከቶችን መመከት ላይ አድርጓል። የአህጉሪቱን ገጽታ መገንባት፣ ትርክቶችን በአዲስ መልክ መቅረጽና የአፍሪካ ህብረት የ2063 አጀንዳም በማህበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ዘንድ ዋነኞቹ የመወያያ አርዕስት ናቸው።
በባለሙያዎች የሚመራው የፓናል ውይይት የሰው ሰራሽ አስተውሎትን (AI) የለውጥ አቅም የሚተነትን ሲሆን፣ ቴክኖሎጂው ለኢኮኖሚ እድገትና ለማህበራዊ ፍትህ ያለውን ፋይዳ በጥልቀት ይቃኛል። የሰው ሰራሽ አስተውሎትን (AI) ተራ የቴክኖሎጂ ውጤት ብቻ ሳይሆን፣ አፍሪካ የራሷን ታሪክ በራሷ አንደበት እንድትተርክ የሚያስችል የለውጥ ሞተር ነው። ውይይቱም ዲጂታል ፈጠራ ለአካታችነት፣ ለበጎ ተግባርና ለአህጉሪቱ ድምጾች መጠናከር የሚኖረውን የማይተካ ሚና ያጎላል።
በተመሳሳይ፣ የፓናል ውይይቶቹ የአፍሪካን ዲጂታል ድምፅ በማጠናከር ረገድ ያሉ እድሎችንና አሉታዊ አመለካከቶችን ለማስወገድ የሚረዱ ስልቶችን ይቃኛሉ። ተጽዕኖ ፈጣሪዎች፣ የሚዲያ ስትራቴጂ ባለሙያዎችና የባህል አምባሳደሮች፤ እውነተኛ ታሪኮችን በማጋራትና ኃላፊነት የተሞላበት የሚዲያ አጠቃቀምን በመከተል የዓለምን ግንዛቤ መቀየር በሚቻልባቸው መንገዶች ላይ ይመክራሉ።
የጉባኤው እያንዳንዱ እንቅስቃሴ ዓላማውን ያጠናክራል፡ የአፍሪካ ትርክት የሁላችንም የጋራ ሃላፊነት ነው የሚለውን እሳቤ። የጋራ መግባባቱም በግልጽ የሚታይ ነው። የዲጂታል መድረኮች ለታለመለት አላማ ጥቅም ላይ ሲውሉ፣ የተገለሉ ወገኖችን ድምጽ የሚያሰሙና የአፍሪካን ብዝሃነትና የፈጠራ አቅም የሚያሳዩ ጠንካራ መሳሪያዎች ይሆናሉ።
ጉባኤው ወደ ማጠቃለያው እየተቃረበ ቢሆንም፣ በተጽእኖ ፈጣሪዎቹ ላይ የሚታየው ተነሳሽነት እና ፍላጎት ደምቆ ቀጥሏል። ተሳታፊዎቹ ሃሳብን ከመለዋወጥ ባለፈ፣ የአፍሪካን እውነተኛ፣ ኩሩ እና ጽኑ ታሪክ ዳግም ለመጻፍ ለሚደረገው ዓለም አቀፋዊ ንቅናቄ መሰረት እየጣሉ ይገኛሉ።
በሚሊየን የሚቆጠሩ ተከታዮች ያሏቸው ተጽዕኖ ፈጣሪዎች አህጉራዊ ኩራትን የሚያጎሉና የተሳሳቱ ግንዛቤዎችን የሚቀይሩ ታሪኮችን ለማጋራት ቃል እየገቡ ሲሆን፤ ፖሊሲ አውጪዎች ደግሞ እነዚህን አዳዲስ ትርክቶች በሀገር አቀፍ እና በአህጉራዊ ማዕቀፎች ውስጥ ለማካተት ስትራቴጂካዊ ዝግጅት እያደረጉ ይገኛሉ።
አሁን እየተደረጉ ያሉት ውይይቶች ይህ ጉዞ የረጅም መንገድ መጀመሪያ መሆኑን የሚያሳዩ ናቸው። በአዲስ አበባ ሰማይ ስር የሚንፀባረቀው ንቁ ተሳትፎ እና ራዕይ፤ አፍሪካ ማንነቷን ለዓለም የምታበስርበትን ድምፅ ይበልጥ ያጠነክረዋል። እያንዳንዱ የሃሳብ ልውውጥ እና አብሮነት፤ አህጉሪቱ የገዛ እጣ ፈንታዋን ለመወሰን ያላትን ጽኑ አቋም የሚመሰክሩ ታሪካዊ አሻራዎች ናቸው።
የመጀመሪያው የማህበራዊ ሚዲያ ተጽእኖ ፈጣሪዎች ጉባኤ (ASMIS2026) በፐልስ ኦፍ አፍሪካ እና በኤጂኤ ቴክ ኢንተርፕራይዝ የጋራ ትብብር የተዘጋጀ ነው።