ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርታማነት ዓለም አቀፍ የንግድ ሚዛንን የሚያስጠብቅ አቅም እየገነባ ነው 

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 28/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርታማነት ዓለም አቀፍ የንግድ ሚዛንን የሚያስጠብቅ አቅም እየገነባ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ሀሰን መሐመድ ገለጹ።   

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከሚያዝያ 25 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆየውን 4ኛው ''ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት'' ኤክስፖ መርቀው መክፈታቸው ይታወቃል።

በአራተኛ ቀን ቀጥሎ በዋለበት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖ ጎን ለጎን ፈጣን የኢንዱስትሪ  ዕድገትን ማፋጠን በሚያስችሉ ተቋማት ግንባታ ዙሪያ የባለድርሻ አካላት የፓናል ውይይት ተካሂዷል።


 

የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ሀሰን መሐመድ በዚህ ወቅት፤ የኢንዱስትሪ ምርታማነት ለሀገር ዕድገት ቁልፍ ሚና እንዳለው ገልጸዋል።

የኢትዮጵያን የኢንዱስትሪ ምርታማነት በማሳለጥ ዘርፉ ለኢኮኖሚ ዕድገት የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ የሚያጎልብት ጠንካራ ተቋምና አሰራር መገንባት እንደሚያስፈለግ ገልጸዋል።

የኢንዱስትሪ ዘርፍ ምርታማነትና የኢንቨስትመንት ምኅዳርን የሚያጠናክር የፖሊሲና የአሰራር ማሻሻያ መደረጉን ተናግረዋል።

በዚህም በኢንዱስትሪ ዘርፍ የተደረጉ የፖሊሲ ለውጦች  ምርታማነትን በማጠናከር ዓለም አቀፍ የንግድ ሚዛንን የሚያስጠብቅ አቅም እየተፈጠረ መሆኑን አንስተዋል።

በቀጣይም ባለድርሻ ተቋማት የኢንዱስትሪ ዕድገትን ለማፋጠን ቅንጅትና ትብብርን የሚያጠናክር ገንቢ ሚና መወጣት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።

ለዘርፉ ዕድገት አቅም የሚሆን ብቁ ሰው ሃብት፣ የሕግና የአሰራር ሥርዓት በመፍጠር በሁሉም መስክ በትብብር መስራት እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል።

የፌዴራል ፐብሊክ ሰርቪስ ምክትል ኮሚሽነር አልማዝ መሰለ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያን የኢንዱስትሪ ምርታማነት የሚያስቀጥል ተቋም እየተገነባ መሆኑን ገልጸዋል።


 

በቀጣይም የኢንዱስትሪ ምርታማነትን በግልጽ አሰራርና በኃላፊነት መርህ መምራት የሚያስችል ቅንጅታዊ አሰራርን ለማጠናከር በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።

የምጣኔ ሃብት ባለሙያው ቆስጠንጢኖስ በርኸተስፋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢንዱስትሪ ዕድገትን ለማፋጠን ግልፀኝነትን ከተጠያቂነት ጋር አጣጥሞ መምራት የሚያስችል አሰራር ያስፈልጋል ብለዋል።


 

በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ የተቋማትን ግልፀኝነት የሚያሰፍን የዲጂታል አሰራር ሥርዓት በመዘርጋት የጀመረችው የዕድገት ጉዞ የሚደነቅ መሆኑን ገልጸዋል።

በቀጣይም የኢንዱስትሪ ተዋናዮች በዘርፉ ለሚነሱ የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች አፋጣኝ መፍትሔ የሚሰጥ የድጋፍና ክትትል ሥራን አጠናክረው መቀጠል እንደሚገባቸው መክረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም