ሀዋሳ ከተማን ተወዳዳሪና ተመራጭ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ውጤት እያስገኙ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ሀዋሳ ከተማን ተወዳዳሪና ተመራጭ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ውጤት እያስገኙ ነው
ሀዋሳ ፤ ሚያዝያ 28/2018 (ኢዜአ)፦ ሀዋሳ ከተማን ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ውጤት እያስገኙ መሆኑን የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ።
የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻን በማልማትና ከአካባቢው መስህቦች ጋር በማስተሳሰር ሀይቁን የቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ የታሰበው የሀይቅ ዳርቻ ልማት ዲዛይን ይፋ ተደርጓል ።
ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ በወቅቱ እንደገለጹት፤ ከተማዋን ለኑሮ፣ ለስራ፣ ለቱሪዝምና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ ለማድረግ የተከናወኑ የልማት ስራዎች ውጤት እያስገኙ ነው።
የልማት ስራዎቹ ከተማዋ ሀገር አቀፍ ስብሰባዎችን፣ ስፖርታዊ ውድድሮችና ሌሎች ኹነቶችን በማስተናገድ ተመራጭ እንድትሆን አድርገዋታል ብለዋል።
የሀዋሳ ከተማን ለኑሮ ምቹና የቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ በሚደረገው ጥረትም ህዝቡንና ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኝ አቶ ደስታ ገልጸዋል።
በተለይም የኮሪደር ልማት ሀዋሳ የተቸረችውን የተፈጥሮ ውበት አጉልቶ ማውጣት መቻሉን የጠቆሙት ርዕሰ መስተዳድሩ የተሰሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አመላክተዋል።
ዛሬ ይፋ የተደረገው የሀይቅ ዳርቻ ልማት ተጨማሪ ውበትና የተወዳዳሪነት አቅም ለመፍጠር ያለመ መሆኑን ጠቁመው ለተግባራዊነቱ በትብብር እንደሚሰራ አመላክተዋል።
የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው እንዳሉት፤ በሀዋሳ ከተማ የተጀመሩ የልማት ስራዎች ተጠናክረው ቀጥለዋል።
ህዝብን በማስተባበር የተሰራውና የሥራ ባህልን የቀየረው የኮሪደር ልማት የዚሁ አካል መሆኑን አንስተዋል።
በዚህም ከተማዋ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ማዕከል መሆን መቻሏን ጠቁመዋል።
በመርሀ ግብሩ ላይ የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሃም ማርሻሎ፣ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የትምህርት ቢሮ ሀላፊ አቶ በየነ በራሳን ጨምሮ ሌሎች የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና ባለሀብቶች ተገኝተዋል።