ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግርን በማፋጠን ረገድ የላቀ ሚና እየተጫወተ ይገኛል  

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 28/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግርን በማፋጠንና የኢንቨስትመንት ስኬትን በማረጋገጥ ረገድ የላቀ ሚና እየተጫወተ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ሀሰን መሐመድ ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከሚያዝያ 25 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆየውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖ መርቀው መክፈታቸው ይታወቃል፡፡ 

በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ ቀደም ሲል ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ስኬታማ ተግባራት ተመዝግበዋል።  

በተለይም የአምራች ኢንዱስትሪዎች አማካይ የማምረት አቅም ከ47 በመቶ ወደ 67 በመቶ ከፍ ማለቱና ባለፉት አራት ዓመታት ብቻ ከ2 ሺህ 800 በላይ አዳዲስ ኢንቨስትመንቶችን መሳብ መቻሉ የዘርፉ ዕድገት ማሳያ ተደርጎ ተወስዷል።  

በተያዘው በጀት ዓመት የመጀመሪያ ዘጠኝ ወራት ውስጥ ብቻ በሀገር ውስጥ ተኪ ምርቶች አማካኝነት ከ4 ነጥብ 85 ቢሊየን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ማዳን መቻሉን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስረድተዋል። 

የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ሀሰን መሐመድ እንዳሉትም፣ ኤክስፖው መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግርን በማፋጠን ረገድ ቁልፍ ሚና ይጫወታል፡፡ 

የዘርፉን አስተዋጽኦ ዘላቂ ለማድረግ መሰረታዊ የፖሊሲ ማሻሻያዎችና ምቹ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፤ በተለይም በኢንቨስትመንት ረገድ ትልቅ ስኬት መመዝገቡን ገልጸዋል። 

ይህም የሀገሪቱን የወደፊት ኢኮኖሚ በጽኑ መሠረት ላይ ለመገንባት የሚያስችሉ የፋይናንስና የፖሊሲ ድጋፎች ውጤታማ በሆነ መንገድ እየተተገበሩ መሆናቸውን ያረጋግጣል ብለዋል። 

ኤክስፖው የሀገር ውስጥና የውጭ ገበያ ትስስርን በማጠናከር እንዲሁም የቴክኖሎጂ ሽግግርን በማፋጠን፣ የኢንዱስትሪውን ዕድገት ወደ ላቀ ደረጃ እያሸጋገረ ይገኛል ብለዋል።  

በተጨማሪም የውጭ ምንዛሬን በማዳንና ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት፣ በራስ አቅም የመቆም የኢኮኖሚ አርበኝነትን እያረጋገጠ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡  

ኢንዱስትሪው የሚፈልገውን በዕውቀትና ክህሎት የሰለጠነ የሰው ኃይል ለማፍራትም ከተለያዩ የትምህርትና የሥልጠና ተቋማት ጋር በተቀናጀ መልኩ ሰፊ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። 

ፍጥነትን፣ ፈጠራንና የዝላይ መርህን በመጠቀም በትንሽ ወጪ ከፍተኛ ምርት በማምረት፣ የኢንዱስትሪውን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። 

በአሁኑ ወቅት በኤክስፖው አማካኝነት በርካታ አምራቾች ከግልና ከመንግሥት ተቋማት ጋር ጠንካራ የገበያ ትስስርና የሥራ ስምምነቶችን በመፍጠር ላይ ይገኛሉ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም