ቀጥታ፡

ከ43 ሚሊዮን በላይ ዜጎች ፋይዳ ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ አውጥተዋል

ኮምቦልቻ ፤ ሚያዝያ 28/2018 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ከ43 ሚሊዮን በላይ ዜጎች ፋይዳ ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ ማውጣታቸውን የፋይዳ ዲጂታል ብሔራዊ መታወቂያ ፕሮጀክት ዳይሬክተር ዮዳሄ አርዓያስላሴ ገለፁ።

በኮምቦልቻ ከተማ ፋይዳ ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ አፈጻጸም ያለበት ሁኔታ ላይ  የሚመክር ጉባኤ ተካሄዷል።


 

ዳይሬክተሩ አቶ ዮዳሄ አርዓያስላሴ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፣ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያን ለሁሉም ህብረተሰብ ተደራሽ ለማድረግ ያላሰለሰ ጥረት እየተደረገ ይገኛል።

መታወቂያው ለአካታች ኢኮኖሚና የፋይናንስ እድገት፣ ፈጣንና ፍትሃዊ አገልግሎት ለመስጠት፣ ህገ-ወጥነትንና ወንጀልን ለመከላከል ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ገልጸዋል።

ይህንኑ ጠቀሜታ በመገንዘብም እንደ ሀገር እስካሁን ከ43 ሚሊዮን በላይ ዜጎች መታወቂያውን ማውጣታቸውን ነው የተናገሩት።

በ2020 ዓ.ም መታወቂያውን 115 ሚሊዮን ለሚደርሱ ዜጎች ተደራሽ ለማድረግ መታቀዱን ነው ያመለከቱት።

በዛሬው  እለት የተካሔደው መድረክ አላማም እስካሁን የነበሩ ጥንካሬዎችን ለማስቀጠልና ድክመቶችን በማረም በቀጣይ የላቀ አፈጻጸም ለማስመዝገብ ያለመ ነው ብለዋል።

የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ በክልሉ ለፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ አተገባበር ተገቢውን ድጋፍና ክትትል እየተደረገ ይገኛል።


 

መታወቂያው ሀገራዊ መለያ ከመሆኑ ባሻገር የተቀላጠፈ እና ፍትሀዊ አገልግሎትን ለመስጠት፣ ወንጀልን ለመከላከልና ተጠያቂነትን ለማስፈን የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል።

መታወቂያውን ከተቋማት ጋር በማስተሳሰርና በማቀናጀት አተገባበሩን ለማሳለጥ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤት እየተመዘገበ በመሆኑም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ነው የተናገሩት።

በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል የከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሀመድ(ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የፋይዳ መታወቂያ  ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ትግበራ እየተደረገ ያለውን ጥረት የሚያፋጥን ነው ብለዋል።

በቀጣይም ተከታታይ ግንዛቤዎችን በመፍጠር ሁሉም ዜጎች ፋይዳ መታወቂያን እንዲያወጡና ተጠቃሚ እንዲሆኑ አመራሩ በትኩረት እንደሚሰራም ነው ያረጋገጡት።


 

በዞኑ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ነዋሪዎች መታወቂያውን ማውጣት ችለዋል ያሉት ደግሞ የደቡብ ወሎ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አሊ ይማም ናቸው።

ሁሉም ዜጎች ፋይዳ መታወቂያን እንዲወስዱ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው፣ አመራሩም ህብረተሰቡን በማስተባበር ጭምር  እየሰራ ይገኛል ብለዋል።

በመድረኩም የፌዴራል፣ የክልል፣ የዞንና የከተማ አመራሮችና የዘርፉ ባለሙያዎች ተሳትፈዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም