ቀጥታ፡

የበጋ ስንዴ ልማት አመርቂ ውጤት እያስመዘገበ ነው -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 28/2018 (ኢዜአ)፦ መሬት ጦም ማደር የለበትም በሚል ጽኑ እምነት የተጀመረው የበጋ ስንዴ ልማት አስደማሚ ውጤት እያስመዘገበ እንደሚገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዛሬው ዕለት በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ሱሉልታ ወረዳ በ2 ሺህ 150 ሄክታር መሬት ላይ የለማ የስንዴ ማሳን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በጉብኝታቸው ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ መንግሥት በግብርናው ዘርፍ በወሰዳቸው ስትራቴጂካዊ እርምጃዎች እየተገኙ ያሉ ውጤቶች አመርቂና ለቀጣይ ሥራዎች ስንቅ የሚሆኑ ናቸው ብለዋል።

የበጋ እርሻና የበጋ ስንዴ ልማት በኢትዮጵያ ውስጥ የተለመደ እንዳልነበርም ጠቅላይ ሚኒስትሩ አንስተዋል።

መሬት ጦም ማደር የለበትም፤ ከልመና ራሳችንን መገላገል አለብን፤ ሊታረስና ሊለማ የሚችል መሬት መታረስ አለበት በሚል ጽኑ እምነት የበጋ ስንዴ ልማት መጀመሩን አብራርተዋል።

የበጋ ስንዴ ልማት ጅማሮው ፈታኝ ቢሆንም፤ አሁን ላይ ሥራው አስደማሚ ውጤት እያስመዘገበ መምጣቱን ተናግረዋል።

ኢትዮጵያ ከዓመታት በፊት ስንዴን ከውጭ የምታስገባ ብቻ ሳይሆን፤ አነስተኛ ምርት ካላቸው አገራት መካከል ትመደብ እንደነበርም ገልጸዋል።

ባለፈው ክረምት 4 ነጥብ 4 ሚሊየን ሄክታር፣ በዘንድሮው በጋ 3 ነጥብ 8 ሚሊየን ሄክታር በድምሩ ከ8 ሚሊየን ሄክታር በላይ መሬት ላይ ስንዴ መታረሱን ገልጸዋል።

በአጠቃላይ ከ330 ሚሊየን ኩንታል በላይ የስንዴ ምርት መገኘቱንና ይህም ኢትዮጵያን ስንዴ በማምረት ከአፍሪካ በግንባር ቀደምትነት የሚያስቀምጣት መሆኑን አመልክተዋል።

ባለፈው ዓመት ከክረምትና በጋ እርሻ 280 ሚሊየን ኩንታል ስንዴ ምርት መገኘቱን አስታውሰው፤ የዘንድሮው ምርት ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ50 ሚሊየን ኩንታል ብልጫ እንዳለው አብራርተዋል።

የተገኘው ከፍተኛ የምርት ልዩነት ከታየባቸው አካባቢዎች አንዱ የሰሜን ሸዋ ዞን መሆኑን ጠቅሰው፤ የማይታረስ መሬት በማረስ በተከናወኑ ተግባራት የስንዴ ምርታማነት ማደጉን ጠቁመዋል።

የስንዴ ልማቱ ወንዞችን በመጥለፍና የክረምት ዝናብን በማቆር መከናወኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በቀጣይም ምርታማነትን ለማስፋት በዞኑ በልዩ ትኩረት እንደሚሠራ መረዳታቸውን ተናግረዋል።

በሰሜን ሸዋ ዞን አርሶ አደሮች በምርታማነት ማደግ ምክንያት የገቢ አቅማቸው እየጨመረ መምጣቱንም ጠቅሰዋል።

የምርታማነትና የገቢ የመሰብሰብ አቅም ማደግ፤ አርሶ አደሮች የተሻለ ኑሮ እንዲመሩ ማድረጉን ም አንስተዋል።

የሰሜን ሸዋ ዞን ተሞክሮ በትጋትና ሀብትን በአግባቡ በመጠቀም ትልቅ ውጤት ማምጣት እንደሚቻል ማሳያ ነው ብለዋል።

አሁንም በኢትዮጵያ ስንዴን በማምረትና ቴክኖሎጂን በመጠቀም ከተሠራ፤ ምርታማነቱን በከፍተኛ ደረጃ ማሳደግ እንደሚቻል አስገንዝበዋል።

ለዚህ ስኬት አርሶ አደሮች፣ የግብርና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎችና አመራሮች በትጋት መሥራት እንዳለባቸውም አሳስበዋል።

በግብርናው ዘርፍ የተወሰደው እርምጃ እንደ ሌሎች መስኮች ውጤታማ፣ አመርቂና አዋጭ ሆኖ መገኘቱን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አሁን ላይ የማደግ አቅሙ ሰፊ እንደሆነም አንስተዋል።

በአጠቃላይ የታየው ሥራ ኢትዮጵያ ትልቅ ተስፋ እንዳላትና የምናልማትን ሀገር ለመፍጠር የሚያስችል መሠረት በሚገባ እየተጣለ መሆኑን የሚያሳይ ነው ብለዋል።

ሁሉንም ቀንና ወቅት መጠቀም አለብን፤ ለማምረት፣ ለመሥራትና ለመልፋት፤ ለመብላት ብቻ ሳይሆን ለማብላትና ለመርዳትም ጭምር መጠቀም ይኖርብናል ሲሉም አሳስበዋል።

በሥራና በልማት ሂደት የሚገጥሙ ፈተናዎችን በድል እንሻገራለን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ለዚህም ሁሉም ዜጋ በትጋት እንዲሠራ ጥሪ አቅርበዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም