ቀጥታ፡

በክልሉ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለኢንዱስትሪ ግብዓት፣ ለፍራፍሬና ለቡና ችግኞች ትኩረት ተሰጥቷል

ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 28/2018(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምግብ ዋስትናን ለሚያረጋግጡ፣ ለኢንዱስትሪ ግብዓት፣ ለፍራፍሬና ለቡና ችግኞች ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ገለጸ።

ቢሮው በክልሉ በሚከናወነው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ንቅናቄ ዙሪያ ዛሬ መግለጫ ሰጥቷል።

የቢሮው ምክትልና የተፈጥሮ ሃብትና የደን ልማት ዘርፍ ሃላፊ አበባየሁ በየነ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ በክልሉ በየዓመቱ በንቅናቄ የሚመራ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ይከናወናል ብለዋል፡፡

በዚህም በክልል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምግብ ዋስትናን ለሚያረጋግጡ፣ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚውሉ፣ ለፍራፍሬና ለቡና ችግኞች ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል።

በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።

ለዘንድሮው ተከላ ከተዘጋጁት ችግኞች 50 በመቶው የፍራፍሬ ችግኝ መሆኑን ጠቅሰው አቮካዶ ቀዳሚ መሆኑንና ፓፓያና ሌሎች ፍራፍሬዎችም እንደሚገኙበት ገልጸዋል።

የተያዘውን የቤተሰብ ብልፅግና የማረጋገጥ ዕቅድ ለማሳካት አጋዥ የሆነውን የእንስሳት ሃብት ልማትን ለማሳደግ የእንስሳት መኖ ተከላም ትኩረት እንደተሰጠው አስረድተዋል።

በክልሉ ደጋማ አካባቢዎች ያለውን የቀርከሃ ልማት ማስፋፋት የሚያስችሉ የቀርከሃ ችግኞችን በማዘጋጀት ለስራ እድል ፈጠራና ለኢንዱስትሪ ግብዓት ለማዋል መታቀዱን አመልክተዋል።

በ416 የመንግስትና የአርሶ አደር ችግኝ ጣቢያዎች ህብረተሰቡን ያሳተፈ የችግኝ ማፍላት ስራ መጠናቀቁን የጠቀሱት ሃላፊው በተከላው ከ27 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት እንደሚሸፈንም ተናግረዋል፡፡

በክልሉ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የአረንጓዴ አሻራ ልማት የደን ሽፋኑን ከማሳደግ ባለፈ የአፈር ለምነትን በመጠበቅ ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ማድረጉን ገልጸዋል፡፡

የተራቆቱ መሬቶች በተከላ መርሃ ግብር እንዲለሙ በማድረግ በእንስሳት እርባታ ለተደራጁ ማህበራት የስራ እድል መፈጠሩንም ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም