የአዲስ አበባ ሰው ተኮር ፕሮጀክቶች የነዋሪዎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል - ኢዜአ አማርኛ
የአዲስ አበባ ሰው ተኮር ፕሮጀክቶች የነዋሪዎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 28/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ሰው ተኮር የልማት ፕሮጀክቶች የነዋሪዎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ተጨባጭ ውጤት ማምጣታቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በተለያዩ ክፍለ ከተሞች የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደየፍላጎታቸው ተደራጅተው ለሰለጠኑ ወገኖች የመስሪያ ቦታ አስረክበዋል።
በዚሁ ወቅት ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ ከተማ አስተዳደሩ ነዋሪዎችን በፍትሃዊነት የሥራ ዕድል ተጠቃሚ የሚያደርጉ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።
በዚህም ባለፉት የለውጥ ዓመታት የሰው ተኮር የልማት ፕሮጀክቶችን በመቅረፅ በርካታ ዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ በማድረግ ተጨባጭ ውጤት ማምጣት እንደተቻለ ተናግረዋል።
በዛሬው ዕለትም በሰው ተኮር ፕሮጀክቶች የተገነቡ በርካታ የመስሪያ ቦታዎችን ለተጠቃሚዎች ማስተላለፍ እንደተቻለ ገልጸዋል።
በሁሉም ክፍለ ከተሞች እንደየፍላጎታቸው ተደራጅተው ለሰለጠኑ 1ሺህ 278 ኢንተርፕራይዞችና 3ሺህ 889 አንቀሳቃሾች ሼዶችና የመስሪያ ቦታዎች መተላለፋቸውን አስታውቀዋል።
ለሥራ ዕድል ተጠቃሚ ዜጎች የተላለፉ የመስሪያ ቦታዎችና ሼዶችም በአጭር ጊዜ ተገንብተው የተጠናቀቁ መሆናቸውን አንስተዋል።
ሁሉም ዜጋ ተግቶ በመስራትና ድኅነትን በማስቀረት የሀገርን ዘላቂ ዕድገት ማፋጠን እንደሚገባው አስገንዝበዋል።
የመስሪያ ቦታ የተሰጣቸው ዜጎችም እራሳቸውን በመለወጥ የስኬት ተምሳሌትነትን በተግባር በማረጋገጥ የኢኮኖሚ ዕድገት አቅም መሆን እንደሚኖርባቸው ጠቁመዋል።
በቀጣይም የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።