መንግስት ለተኪ እና ወጪ ምርት የሰጠው ትኩረት ውጤታማ አድርጎናል - አምራች ኢንዱስትሪዎች - ኢዜአ አማርኛ
መንግስት ለተኪ እና ወጪ ምርት የሰጠው ትኩረት ውጤታማ አድርጎናል - አምራች ኢንዱስትሪዎች
ወልቂጤ፤ ሚያዝያ 28/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አምራች ኢንዱስትሪውን በመደገፍና በማብቃት እንዲሁም ለተኪ እና ወጪ ምርት የተሰጠው ትኩረት ውጤታማ እንዳደረጋቸው በዘርፉ የተሰማሩ አምራቾች ገለፁ።
መንግስት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በማምረቻው ዘርፍ ለተሰማሩ ባለሀብቶች የንግድ ከባቢን ምቹ የማድረግ፣ የመሰረተ ልማት አቅርቦት የማሟላትና የፖሊሲ ማሻሻያዎችን የማድረግ ስራዎች በስፋት እያከናወነ ይገኛል።
በተጨማሪም ለሀገር ውስጥ አምራቾች ልዩ የድጋፍ ፓኬጆችን በማዘጋጀት አምራቾችን እያበረታታ ነው።
ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሚገኙ አምራቾች፤ መንግስት አምራች ኢንዱስትሪውን በመደገፍና በማብቃት ለተኪ እና ወጪ ምርት ዕድገት የሰጠው ትኩረት ውጤታማ እንዳደረጋቸው ገልጸዋል።
በቡታጀራ ከተማ የሚገኘው የደስታ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ ዋና ስራ አስኪያጁ ያሬድ ወልዴ እንዳሉት፤ ፋብሪካው ለአምራች ኢንዱስትሪው የተመቻቸውን እድል በመጠቀም በዓለም አቀፍ ገበያ ተፈላጊ የሆኑ ምርቶችን እያመረተ ይገኛል።
በዚህም ከፍተኛ የሀገር ውስጥ የጥጥ ምርትን በግብዓትነት በመጠቀምና የማምረት ስራውን አጠናክሮ በመቀጠል የአልባሳት ምርቶችን ለአውሮፓ፣ ለአሜሪካና ለተለያዩ የውጭ ሀገራት ገበያዎች እያቀረበ መሆኑን ተናግረዋል።
ፋብሪካው ከውጭ ከሚገባው በጥራትና በዋጋ የተሻሉ ምርቶችን በማምረት ለሀገር ውስጥ ገበያም እያቀረበ መሆኑን ነው የሚገልጹት።
ከ1 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል በመፍጠር በኢኮኖሚ ተጠቃሚ እንዲሆኑ እያደረገ እንደሆነም አክለዋል።
በቡኢ ከተማ የሚገኘው የብሉ ኤሌፋንት ፋይበር ቦርድ ፋብሪካ ኃላፊ ተወካይ ፍቅር ታደሰ በበኩላቸው፤ መንግስት የመስሪያና የመሸጫ ቦታ፣ የብድር ፣ የመሰረተ ልማት አቅርቦቶችን በማመቻቸቱ ውጤታማ እንድንሆን አድርጎናል ብለዋል።
አሁን ላይ ፋብሪካው ከውጭ ይገባ የነበረ ለህንፃ፣ ለመንገድ ግንባታና ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ ቦርዶችን ለሀገር ውስጥ ገበያ እያቀረቡ መሆኑን አመልክተው በቀጣይም ምርቱን ወደ ውጭ ለመላክ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በፋብሪካው ስራ ከተፈጠረላቸው ከ600 በላይ ሰዎች በተጨማሪ ለግብዓትነት የሚውሉ የእንጨት ምርቶችን የሚያቀርቡ አርሶ አደሮችንም ተጠቃሚ በማድረግ የተሻለ ህይወት እንዲመሩ እያደረገ መሆኑንም አስረድተዋል።
ከውጭ የሚገባውን የፉርኖ ዱቄት በሀገር በመተካት ለማሕበረሰቡ እያቀረቡ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የዳሬም ዱቄት ፋብሪካ ስራ አስኪያጅ ወንድሙ ሀይሌ ናቸው።
ፋብሪካው በቀን ከ400 ኩንታል በላይ የስንዴ ዱቄት በማምረት ለገበያ በማቅረብ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ደምሰው ባቾሬ በበኩላቸው የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በክልሉ የኢንዱስትሪውን ዘርፍ በማነቃቃት የማምረት አቅም እንዲያድግ አስችሏል ብለዋል።
በእንጨትና ብረታብረት፣ በግብርና ምርቶች ማቀነባበር፣ በልብስ ስፌት እንዲሁም በተለያዩ ዘርፎች የተሰማሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች ተኪና ወጪ ምርቶችን በጥራትና በብዛት በማምረት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በዚህም ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን በማጎልበት በኩል የድርሻቸውን እየተወጡ ይገኛሉ ብለዋል።
ክልሉ በተለያዩ ዘርፎች እምቅ አቅም ያለውና ውጤታማ መሆን የሚቻልበት መሆኑን ገልጸውም በኢንዱስትሪው ዘርፍ ለሚሰማሩ ባለሃብቶችም ቀልጣፋ አገልግሎት፣ የለማ መሬትና ሌሎች ድጋፎች እንደሚደረጉም አረጋግጠዋል።