የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የአገሪቱን ዘላቂ ዕድገትና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን ማዕከል ባደረገ መልኩ እየተገነባ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የአገሪቱን ዘላቂ ዕድገትና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን ማዕከል ባደረገ መልኩ እየተገነባ ነው
አዲስ አበባ፣ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፡-የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ የአገሪቱን ዘላቂ ዕድገትና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን ማዕከል ባደረገ መልኩ እየተገነባ መሆኑ ተገለጸ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ካለፈው ሚያዝያ 25 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ግንቦት 30 ቀን ድረስ የሚቆየውን የ"ኢትዮጵያ ታምርት" ኤክስፖ በይፋ መክፈታቸው ይታወቃል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ በዘንድሮው “ኢትዮጵያ ታምርት” ኤክስፖ ላይ የሀገራዊ ርዕያችንን ተጨባጭ ስኬት መመልከት ትልቅ ክብር ነው ብለዋል።
ውጤት ተኮር አመራራችን ከዚህ ቀደም ታይቶ በማይታወቅ የኢንዱስትሪ መስፋፋት መንጸባረቁን ጠቅሰው ይኸውም የአምራች ኢንዱስትሪዎችን አማካይ የማምረት አቅም ከ47 በመቶ ወደ 67 በመቶ ከፍ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል፡፡
ባለፉት አራት አመታት ከ2ሺህ 800 በላይ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንቶችን መሳብ መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡
በዛሬው ዕለትም "በኢትዮጵያ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የአረንጓዴ ሽግግርን ማፋጠን፤መዋቅራዊ ለውጥን ከአየር ንብረት መቋቋም እና ከንግድ ተወዳዳሪነት ጋር ማጣጣም" በሚል መሪ ሐሳብ ውይይት ተካሂዷል፡፡
የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬነሽ መኩሪያ እንደገለጹት፤ በዘርፉ የአረንጓዴ ሽግግርን ለማፋጠንና የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም መዋቅራዊ ለውጥ ለማምጣት በትኩረት እየተሰራ ነው።
የኢንዱስትሪ ልማት የኃይል አቅርቦት በታዳሽ ኃይል ላይ የተመሰረተ መሆኑ ትልቅ ዕድል መሆኑን ጠቅሰው፥ ምርቶች ሲመረቱ የአፈር፣ የውሃ፣ የአየርና የድምጽ ብክለት እንዳያስከትሉ ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ ለሀገር የኢኮኖሚ ምሰሶ እንደመሆኑ መጠን፣ ከተፈጥሮና አካባቢ ጥበቃ ጋር ተስማምቶ መጓዝ ይገባዋል ብለዋል፡፡
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ትምህርት ክፍል የመወያያ ጽሑፍ ያቀረቡት ተባባሪ ፕሮፌሰር ታደለ ፈረደ በበኩላቸው፥ ኢትዮጵያ የዘላቂ ልማት ግቦችን መሠረት አድርጋ እየሠራች መሆኑን ጠቁመዋል።
በኢትዮጵያ የተገነቡት ኢንዱስትሪ ፓርኮች ታዳሽ ኃይልን የሚጠቀሙ በመሆናቸው፣ ከብክለት የጸዳ ምርት እንዲመረትና ለአየር ንብረት የማይበገር የኢኮኖሚ ግንባታ ትልቅ መሠረት እንዲጣል አስችሏል ብለዋል።
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የማኔጅመንት ትምህርት ክፍል የተሳተፉት ኢትዮጵያ ለገሰ (ዶ/ር) በበኩላቸው ኢትዮጵያ በታዳሽ ኃይል ላይ የምታደርገው ጥረት በቀጣይ የአረንጓዴ ማኑፋክቸሪንግ ማዕከል እንድትሆን ያስችላታል ብለዋል።
ምርቶቹ በታዳሽ ኃይል መመረታቸው በርካታ ፋይዳዎች እንደሚስገኝ ጠቅሰው በዋናነት በዓለም ገበያ ላይ ለሥነ-ምህዳር ተስማሚ የሆኑ ምርቶች ያላቸው ተፈላጊነት እየጨመረ በመሆኑ ኢትዮጵያ ተጠቃሚ ትሆናለች ብለዋል።
በተጨማሪም ከአፍሪካ አልፎ ወደ ተለያዩ የዓለም ገበያዎች በስፋት ለመግባትና ተወዳዳሪ ለመሆን እንደሚያግዝ ገልጸዋል።