የለውጡ መንግሥት ኅብረ-ብሔራዊነትን በማጠናከር እድገት እንዲረጋገጥ ሠርቷል - ኢዜአ አማርኛ
የለውጡ መንግሥት ኅብረ-ብሔራዊነትን በማጠናከር እድገት እንዲረጋገጥ ሠርቷል
ይርጋጨፌ፤ ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፡- የለውጡ መንግሥት ኅብረ-ብሔራዊነትን በማጠናከር ፈጣን እድገት እንዲረጋገጥ አበክሮ መሥራቱን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሠ መሥተዳድር አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) ገለጹ።
በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ከተማ "ኢትዮጵያን ወደ ተምሳሌት ሀገር" በሚል መሪ ሐሳብ የብልጸግና ፓርቲ የምርጫ ቅስቀሳ መርሐ-ግብር ተካሂዷል።
አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ ብልጽግና የነገን ትውልድ ታሳቢ ያደረገ ውጤታማ ሥራዎችን አከናውኗል ብለዋል።
የለውጡ መንግሥት ኅብረ-ብሔራዊነትን በማጠናከር ፈጣን እድገት እንዲረጋገጥ አበክሮ መሥራቱን ገልጸው፤ ብልጽግናን በመምረጥ ለውጡን ማስቀጠል እንደሚገባ አመልክተዋል።
የጌዴኦ ዞን ዋና አሥተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የለውጡ መንግሥት የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተለያዩ ተግባራትን ማከናወኑን ጠቁመዋል።
በዞኑ የቡና ልማትን ለማሻሻል በተደረገ ጥረት አማካይ ምርታማነትን በሔክታር 11 ነጥብ 9 ኩንታል እንዲሁም በሞዴል አርሶ አደሮች ማሳ 20 ኩንታል ማድረስ መቻሉንም አንስተዋል።