የሰው ሰራሽ አስተውሎት ያመጣቸውን ውጤቶች በላቀ ሁኔታ ለመጠቀም ሳይንሳዊ መሠረት ያለው ትውልድ መፍጠር ይገባል - ኢዜአ አማርኛ
የሰው ሰራሽ አስተውሎት ያመጣቸውን ውጤቶች በላቀ ሁኔታ ለመጠቀም ሳይንሳዊ መሠረት ያለው ትውልድ መፍጠር ይገባል
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ያመጣቸውን ውጤቶች በላቀ ሁኔታ ለመጠቀም ሳይንሳዊ መሠረት ያለው ትውልድ መፍጠር እንደሚገባ የቀድሞው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስ ሶሳይቲ የበላይ ጠባቂ አቶ ደመቀ መኮንን ገለጹ፡፡
የቀድሞው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስ ሶሳይቲ የበላይ ጠባቂ አቶ ደመቀ መኮንን ለኢዜአ እንዳሉት፤ መንግሥት ሳይንሳዊ ትውልድ መፍጠር የሚያስችል ሥርዓት ገቢራዊ አድርጓል፡፡
በዚህም የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስ ሶሳይቲ ለሳይንስ ዕድገት መሠረት የሚጥሉ ተቋማት እንዲገነቡና በዘርፉ ብቁ ባለሙያዎችን በማፍራት ረገድ ጉልህ አበርክቶ እንዳለው ገልጸዋል፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ የስፔስ ሳይንስ ዘርፍ በፍጥነት እያደገ መምጣቱን ገልጸው፤ አዳዲስ ሁነቶችን የሚመጥን ተወዳዳሪነትን ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስ ሶሳይቲ ለኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስ ዘርፍ ገንቢ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን በመጥቀስ፤ በመንግሥትና በግሉ ዘርፍ ጭምር አጀንዳ መሆን የቻለበትን አውድ ፈጥሯል ብለዋል፡፡
ከዚህ አኳያ መንግሥት ለስፔስ ሳይንስ ዕድገት ወሳኝ የሆኑ የአቅም ግንባታና መሠረተ ልማት ማስፋፊያ ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስ ዘርፍ አቅሙን እያጠናከረ መሆኑን በመግለጽ፤ የእንጦጦ የጠፈር ምርምር ማዕከል (ኦብዘርቫቶሪ) ተደራጅቶ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑንና የላሊበላን በቀጣይ ማጠናከር እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያ እንዲሁም ተቋማትና ግለሰቦች በዓለም ነባራዊ ሁኔታ ተወዳዳሪ ሆነው ለመውጣት ሳይንስ መሠረታዊ መሆኑን ያመለከቱት አቶ ደመቀ፤ ህልምን ለማሳካት ሳይንስን የተመረኮዘ አገርና ማኅበረሰብ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል፡፡
የሰው ሠራሽ አስተውሎት በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ መሆኑን ገልጸው፤ ሳይንስን መሠረት ባደረገው የዓለም እንቅስቃሴ ሰው ሠራሽ አስተውሎት ያመጣውን ዕድል መጠቀም ይገባል ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ ወጣቶች በስታርት አፕ ቴክኖሎጂና በኢንተርፕረነርሽፕ በስፋት እየተሳተፉ መሆኑን በማንሳት፤ ለዚህ የሚሆን ዝግጁ ወጣትና ማኅበረሰብ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል፡፡
በኢትዮጵያ የስፔስ ሳይንስን ለማሳደግ ጥሩ መሠረት እንዳለ በመጥቀስ፤ የተጀመሩ መልካም ጅምሮችን የበለጠ ማላቅ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡