ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግር የሀገር ውስጥ የኢንዱስትሪ ምርታማነትን እያሳደገ ነው

አዲስ አበባ ፤ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግር የሀገር ውስጥ የኢንዱስትሪ ምርታማነትን እያሳደገ እንደሚገኝ ከፍተኛ የዘርፉ ምሁራንና ተመራማሪዎች ገለጹ።

በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል እየተካሄደ የሚገኘው አራተኛው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ዛሬም ቀጥሎ ውሏል።

በሁለተኛ ቀን ውሎው በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር፣ በሰው ኃይል ልማትና በምርታማነት አቅም ዙሪያ ያተኮረ የምክክር መድረክ ተካሂዷል።

በመድረኩም የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሲለሺ ለማ፤ ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ዕድገትን የሚያፋጥን ጠንካራ መሰረት እየጣለች ነው ብለዋል።


 

የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ጠንካራ መሰረቶችም ምርታማነትና የቴክኖሎጂ ሽግግርን በማፋጠን ዓለም አቀፍ የተወዳዳሪ አቅም እየገነባ መሆኑን ገልጸዋል።

የኢንዱስትሪ ምርቶቿንም በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት የትግበራ ሂደት ቀጣናዊ የንግድ ትስስርን አዳዲስ ዕድሎችን እየፈጠረች እንደምትገኝ ተናግረዋል።


 

በተባበሩት መንግስታት የንግድና ልማት ጉባኤ (UNCTAD) የምርታማነት አቅምና ዘላቂ ልማት የአፍሪካ ዲቪዥን ኃላፊ ሙሴ ደለለኝ (ዶ/ር)፤ ኢንዱስትሪ ምርታማነት የዕድገት መሰረት ነው ብለዋል።

በዚህም ኢትዮጵያ የፈጠረችውን የኢንቨስትመንት አስቻይ ምኅዳር የበለጠ በማስፋት ዕድገትን የሚያፋጥን የኢንዱስትሪ ምርታማነት ማጠናከር እንደሚጠበቅባት አስገንዝበዋል።

በኢትዮጵያ የልማት ምርምር ኢንስቲትዩት የድህነት ቅነሳና ዘርፈ-ብዙ ጥናት ተመራማሪ አለበል ባይራው (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር የዕድገት ማሳለጫ መሳሪያ ነው ብለዋል።

በዚህ በኩል ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርታማነትን በማሳደግ ገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት የውጭ ምንዛሬ ወጪን ማስቀረት በሚያስችል ወሳኝ ምዕራፍ እያለፈች መሆኗን ገልጸዋል።


 

በዓለም አቀፍ የዕድገት ማዕከል የኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጅ ቴዎድሮስ መኮንን (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ለኢንዱስትሪ ምርታማነት አቅም የሆነ የሰው ሃይል ያላት ሀገር ናት ብለዋል።

የኢትዮጵያ አብዛኛው ህዝብ በወጣት የዕድሜ ክልል የሚገኝ በመሆኑም የቴክኖሎጂ ሽግግርን ለማፋጠን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም