በባህርዳር ከተማ ጸጋን ወደ በረከት የሚቀይሩ ግዙፍ የቱሪዝም ልማት ፕሮጀክቶች እየተገነቡ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በባህርዳር ከተማ ጸጋን ወደ በረከት የሚቀይሩ ግዙፍ የቱሪዝም ልማት ፕሮጀክቶች እየተገነቡ ነው
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ በባህርዳር ከተማ የቱሪዝም ጸጋዎችን ወደ በረከት የሚቀይሩ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች እየተገነቡ እንደሚገኙ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በባህርዳር ከተማ በ3 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር የሚገነባውን ፎር ፖይንትስ ባይ ሸራተን ጣና የሆቴል ፕሮጀክት ግንባታን አስጀምረዋል።
በታሪካዊው ጣና ሆቴል ባለበት ሥፍራ ላይ በሚድሮክ ኢንቨስትመንት የሚገነባው ይህ ዓለም አቀፍ ሆቴል በ18 ወራት ውስጥ ተገንብቶ እንደሚጠናቀቅ ተገልጿል።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት ለባህርዳር ከተማና ለሀገራችን የቱሪዝም መዳረሻነት ከፍታና ለኢኮኖሚ መነቃቃት ትልቅ ብስራት ነው ብለዋል።
የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በእርሻ፣ በማዕድንና በሌሎች ዘርፎች የሚያስመዘግበው አስደናቂ ስኬት የግሉ ዘርፍ በኢኮኖሚ ዕድገት የሚያበረክተውን ከፍተኛ ሚና በተግባር የሚያረጋግጥ መሆኑን ገልጸዋል።
በተለይም የኢንቨስትመንት ግሩፑ በፈታኝ ወቅት ቀድሞ በመገኘትና ክፍተቶችን በመሙላት በኩል የላቀ ተምሳሌትነት መገለጫ እንደሆነም ተናግረዋል።
በባህርዳር ግንባታው የተጀመረው ሆቴል ሲጠናቀቅም ጸጋን ወደበረከት በመቀየር ኢትዮጵያ ዘመኑን የዋጀና ዘላቂ ኢኮኖሚ ለመገንባት በጀመረችው ጉዞ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን አንስተዋል።
በተለይም በአካባቢው ካሉ የተፈጥሮና ሠው ሠራሽ የቱሪዝም ፀጋዎች ጋር ተዳምሮ ለባህርዳርና ለአካባቢው ዕድገት ትልቅ ዕድል ይዞ እንደሚመጣም አስረድተዋል።
መንግሥት የኢትዮጵያና ከተሞቿን የቱሪዝም መዳረሻነት ከፍ የሚያደርጉ ትውልድ ተሻጋሪ ፕሮጀክቶች እንዲሳኩ ለማድረግ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።
የፎር ፖይንትስ ባይ ሸራተን ጣና ሆቴል ፕሮጀክት በፍጥነት በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ለማብቃት መትጋት እንደሚገባ አፅንኦት ሰጥተዋል።
የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ጀማል አህመድ በበኩላቸው፥ ኩባንያው መንግሥት የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ለቱሪዝም ዘርፉ መነቃቃት የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ነው ብለዋል።
በባህርዳር የሚገነባውን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ሆቴል በ18 ወራት ውስጥ ለማጠናቀቅ እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
ሚድሮክ በተለያዩ ከተሞች ለኢትዮጵያ ቱሪዝም ዕድገት ገንቢ ሚና የሚወጡ ዘመናዊ ሆቴሎችን እየገነባ እንደሚገኝም አስታውቀዋል።
በ3 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ወጪ የሚገነባው የፎር ፖይንትስ ባይ ሸራተን ጣና ሆቴል በ32 ሺህ 440 ካሬ ሜትር ላይ የሚያርፍ ሲሆን 120 ዘመናዊ መኝታ ክፍሎችና አራት ዓለም አቀፍ ሬስቶራንቶች፣ ከ1 ሺህ በላይ ሰዎችን ማስተናገድ የሚችል ትልቅ አዳራሽና የመዋኛ ገንዳን ጨምሮ ሌሎች አገልግሎቶችን አካቷል።