መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀልጣፋ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል-ተገልጋዮች - ኢዜአ አማርኛ
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀልጣፋ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል-ተገልጋዮች
አምቦ ፣ሚያዚያ 26/2018 (ኢዜአ)፦መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መጀመሩ እንግልትን በማስቀረት ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለማግኘት ምቹ ሁኔታ ፈጥሮልናል ሲሉ የአምቦ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ።
በማዕከሉ የመኖሪያ ቤት ግንባታ ፍቃድ ለማውጣት የመጡት አቶ ፍቃዱ ባይሳ ለኢዜአ እንዳሉት ፤ አገልግሎቱ በቴክኖሎጂ የተደገፈና ከወረቀት ንክኪ የፀዳ በመሆኑ ጉዳያቸውን በአጭር ጊዜ ውስጥ ማጠናቀቅ ችለዋል።
በተለይ ሁሉንም ዓይነት አገልግሎት በአንድ ስፍራ በተሟላና ቀልጣፋ በሆነ አግባብ ማግኘት መቻላቸው ከዚህ በፊት የነበረውን አላስፈለጊ ወጪና እንግልት እንዳስቀረላቸው ነው የሚናገሩት።
የመሬት ይዞታ ባለቤትነት ማረጋገጫ ሰነድ ለሙውሰድ ወደ ማእከሉ መምጣታቸውን የሚናገሩት ወይዘሮ ብርቄ ጣሶ ፤በማዕከሉ የሚፈልጉትን አገልግሎት በፍጥነት ለማግኘት መቻላቸውን ተናግረዋል።
በተለይም በአንድ ቦታ የተሟላና ፈጣን አገልግሎት ማግኘት መቻሉ ከዚህ በፊት ይገጥሙ የነበሩ ችግሮችን እንዳስቀረ ነው ያነሱት።
ጉዳያቸውን በአጠረ ጊዜ ውስጥ በማጠናቀቅ ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘት መቻላቸውን የገለጹት ደግሞ የመኖሪያ ቤት የሊዝ ውል ስምምነት ለመፈጸም ወደ ማእከሉ የመጡት አቶ ጂረኛ ተረፈ ናቸው።
አገልግሎት አሰጣጡም ቀልጣፋ፣ምቹ እና ድካምን ያስቀረ ሆኖ እንዳገኙትም ነው የተናገሩት።
የአምቦ ከተማ አስተዳደር መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ አራርሳ ከበደ በበኩላቸው፤ ማዕከሉ በአንድ ቦታ 107 አገልግሎቶችን መስጠቱ ማሕበረሰቡ ይደርስበት የነበረውን እንግልት ለማስቀረት አስችሏል ብለዋል።
በተለይም በዘርፉ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ይነሱ የነበሩ በርካታ ቅሬታዎችን ለመፍታት እንዳስቻለም ነው የተናገሩት።
በማዕከሉ የአገልግሎት ተደራሽነትን ለማስፋት፣ ግልፅና ቀልጣፋ ለማድረግና የተገልጋዮችን እርካታን በተሻለ መልኩ ለመጨመር በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል።
በማዕከሉ 18 የከተማው ሴክተር ጽህፈት ቤቶች 107 አገልግሎቶችን በተሟላ መልኩ እየሰጡ እንደሚገኙ አስታውቀዋል።