ለኢንቨስትመንት የሚውሉ ሀብቶችን ለማልማት በሚደረገው ጥረት ባለሀብቱ ሚናውን ሊያጠናክር ይገባል - ኢዜአ አማርኛ
ለኢንቨስትመንት የሚውሉ ሀብቶችን ለማልማት በሚደረገው ጥረት ባለሀብቱ ሚናውን ሊያጠናክር ይገባል
ባሕር ዳር፤ ሚያዝያ 26/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ለኢንቨስትመንት የሚውሉ ሀብቶችን ለይቶ በማልማት ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማጎልበት እየተደረገ ባለው ጥረት ባለሀብቱ ሚናውን ሊያጠናክር እንደሚገባ ርዕሠ መሥተዳደር አረጋ ከበደ አሳሰቡ።
በባሕር ዳር ከተማ መሬት ወስደው በኢንቨስትመንት ዘርፍ ከተሰማሩ ባለሃብቶች ጋር የውይይት መድረክ ተካሂዷል።
ርዕሠ መሥተዳድሩ በዚሁ ወቅት፤ ክልሉ በግብርና፣ በማዕድን፣ በቱሪዝም እና በሌሎች ዘርፎች የዕምቅ ሃብቶች ባለቤት በመሆኑ ይህን ሀብት በማልማት ክልሉንና ሀገሪቱን የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ባለሃብቱ ሚናውን ሊያጠናክር እንደሚገባ ገልጸዋል።
በተለይም በግብርና ዘርፍ ክልሉ ለኤክስፖርትና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ምርቶች በብዛትና በጥራት የሚመረትበት በመሆኑ ባለሃብቶች በዘርፉ ተሳትፏቸውን እንዲያጠናክሩም ጠይቀዋል ።
በማዕድን ዘርፍም የኦፓል፣ የወርቅ፣ የብረት፣ የድንጋይ ከሰልና ለሌሎች አገልግሎት የሚውሉ ሃብቶች ባለቤት በመሆኑ፤ ሃብቱን አልምቶ ለመጠቀም ባለሃብቶች በዘርፉ የበለጠ ሊሳተፉ እንደሚገባም አመልክተዋል።
የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው ወደምርት የተሸጋገሩና በግንባታ ላይ የሚገኙ ባለሃብቶች ሥራቸውን በማጠናከር የክልሉን ልማት እንዲያፋጥኑ አሳስበዋል።
የክልሉ መንግሥት በዘርፉ የሚስተውሉ የብድር፣ የኤሌክትሪክ አግልግሎትና የመንገድ መሠረተ-ልማት አቅርቦት ክፍተቶችን ለመቅረፍ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ አረጋግጠዋል።
የባሕር ዳር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው በበኩላቸው፤ አሥተዳደሩ ከተማዋን የቱሪዝምና የኢኮኖሚ ማዕከል ለማድረግ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን አስታውቀዋል።
በከተማዋ አዲስ ለኢንዱስትሪ መንደር የሚሆን ተጨማሪ 300 ሔክታር መሬት በመለየት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ እስካሁን 122 ሔክታር መሬት ተሸንሽኖ ለባለሀብቶች ዝግጁ መደረጉን አስታውቀዋል።
በከተማዋ የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው በተለያዩ ምክንያቶች ሥራ ያቆሙ ባለሃብቶች ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉን ገልፀው፤ ዘንድሮ 23 ፋብሪካዎች ወደማምረት እንዲገቡ መደረጉን አንስተዋል።