ቀጥታ፡

በአማራ ክልል ብቁ የሰው ኃይል በመፍጠር የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰራ ነው

ደሴ ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን የተላመደ ብቁ የሰው ኃይል በማፍራት፣ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ስራና ክህሎት ቢሮ ገለጸ።

ቢሮው ለዘርፉ ቡድን መሪዎችና ባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ስልጠና በኮምቦልቻ ከተማ መስጠት ጀምሯል።


 

በአማራ ክልል ስራና ክህሎት ቢሮ የተቋማት አግባብነትና ጥራት ማረጋገጥ ዳይሬክተር  አቶ ሙላው ልመንህ እንደገለፁት፣ የገበያ ፍላጎትንና የመልማት ፀጋን መሰረት በማድረግ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት በመከናወን ላይ ናቸው።

ለዚህም ቴክኖሎጂን የተላመደ ብቁ የሰው ሃይል በመፍጠር የህብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

ስልጠናው በተሻሻለው የቴክኒክና ሙያ ስትራቴጂ፣ በፖሊሲ፣ በደንብና አዳዲስ እሳቤዎች ዙሪያ ግንዛቤ ከመፍጠር ባለፈ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምና በፈጠራ ሥራዎች ላይ እውቀት የሚያስጨብጥ ይሆናል ብለዋል።

በዚህም ሁሉም ባለድርሻ አካላት ዓለም የደረሰበትን በቴክኖሎጂ የተደገፈ የአገልግሎት አሰጣጥ ተረድቶ ተፎካካሪና ተወዳዳሪ ለመሆን መነሳሳት የሚፈጥርለት ነው ብለዋል።

በቴክኖሎጂው ዘርፍ ባለፉት ዓመታት አበረታች ውጤቶች መገኘታቸውን ጠቁመው በስራ እድል ፈጠራውም ዙሪያ የተሻለ ማከናወን መቻሉን አስረድተዋል።


 

በዋግኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን ስራና ክህሎት መምሪያ የኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን ተሞክሮ ቅመራ ባለሙያ ወይዘሮ እምዬ ጌታቸው በበኩላቸው፣ አሰራሩን በቴክኖሎጂ በማስደገፍ የተሻለ ለመስራት ጥረት እየተደረገ ነው ብለዋል።

ስልጠናው እውቀታቸውንና ክህሎታቸውን በማሰደግ ብቁና ተወዳዳሪ ለመሆን እንደሚያግዛቸው ጠቁመው፣ ስልጠናውን በአግባቡ ተከታትለው የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።


 

የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ስራና ክህሎት መምሪያ የትምህርትና ስልጠና ቡድን መሪ አቶ ዓሊ ኢብራሂም በሰጡት አስተያየት በቴክኖሎጂ ታግዘን ለዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ስልጠናው አስፈላጊ ነው ብለዋል።

ለአንድ ሳምንት በሚቆየው በዚሁ ስልጠና የክልል፣ የዞንና የከተማ፣ የፖሊ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ አመራሮች፣ ቡድን መሪዎች፣ ባለሙያዎችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ነው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም