የምርምር ኢንስቲትዩት የኢትዮጵያን የሕክምና ምርምር ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የምርምር ኢንስቲትዩት የኢትዮጵያን የሕክምና ምርምር ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ነው
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦በአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት የተገነባው ዘመናዊው የምርምር ላቦራቶሪ ኮምፕሌክስ የኢትዮጵያን የሕክምና ምርምር ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ የልህቀት ማዕከል መሆኑን የአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተቋሙን በመረቁበት ወቅት እንደገለጹት፣ በአርማወር ሐንሰን የምርምር ተቋም ቅጥር ግቢ ውስጥ የተገነባው ይህ ዘመናዊ ማዕከል ከመሠረተ ልማት ግንባታ ባለፈ፣ ራሷን የቻለችና ጤናማ የሆነች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የሚተጋ የላቀ የዕውቀት ማዕከል ነው።
ተቋሙ ምርምርን ወደ ፖሊሲ፣ ፈጠራን ደግሞ ወደ ተግባራዊ መፍትሔ በመቀየር፤ በመድኃኒት ምርት ራሳችንን ለመቻል፣ ዘላቂ የጤና ደህንነትን ለማረጋገጥ እና ከሁሉም በላይ ደግሞ እስካሁን ያስመዘገብናቸውን ስኬቶች ይበልጥ ለማሳደግ የሚረዳ ትልቅ እርምጃ ነው ሲሉ ገልጸዋል።
ይህ ማዕከል በኢትዮጵያና በአፍሪካ የሳይንስ ሥነ-ምሕዳር ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ዘመናዊ የምርምር ተቋም መሆኑንም አረጋግጠዋል።
የአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኢንስቲትዩቱ በበሽታዎች ምርምር፣ ምርመራ እና በወረርሽኝ መልክ የሚከሰቱ የጤና ስጋቶችን ለመለየት የሚያስችል ትልቅ አገራዊ አቅም ገንብቷል።
ተቋሙ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ እና በሰለጠነ የሰው ኃይል ታግዞ የኢትዮጵያን የሕክምና ምርምር ወደ ላቀ ከፍታ የሚያሸጋግር ሥራ እያከናወነ መሆኑንም ጠቁመዋል።
በቅርቡ የተመረቀው የምርምር ኮምፕሌክስ ዘመናዊ የላቦራቶሪ መሠረተ ልማትና የሰለጠነ የሰው ኃይልን ያካተተ መሆኑን አመልክተው፤ በኢትዮጵያ ያለውን የሕክምና ምርምር ደረጃ ማሳደጉን ገልጸዋል።
አዳዲስና ነባር በሽታዎችን በትክክል የመለየት አቅሙም ለሕክምናው ዘርፍ ትልቅ እገዛ እያደረገ ይገኛል ብለዋል።
በወረርሽኝ መልክ የሚከሰቱ በሽታዎችን በምርምር ለመተንተንና ለመለየት፣ እንዲሁም የሕዝብ ጤና ደህንነትን ለመጠበቅ ዝግጁነቱን ማጠናከሩን ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል።
ኢንስቲትዩቱ የሚከተላቸው የምርምር ስልቶች ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ መሆናቸው ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለምስራቅ አፍሪካ ቀጣናም ትልቅ ፋይዳ እንዳለው አክለዋል።
አዲሱ የላቦራቶሪ ኮምፕሌክስ በርካታ ላቦራቶሪዎችን በአንድ ላይ የያዘና ትልቅ አገራዊ አቅም የፈጠረ መሆኑን ገልጸው፤ በተለይም የዘርመል (Genetic) ትንተና ለማከናወን የሚያስችል አቅሙ ከዚህ ቀደም ወደ ውጭ አገር ተልከው የሚሠሩ ምርመራዎችን በአገር ውስጥ ለማከናወን ያስችላል ብለዋል።
በማዕከሉ የተለያዩ የምርምርና የትንተና ሥራዎችን በአገር ውስጥ አቅም ለመሥራት የሚያስችሉ የተለያዩ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች መሟላታቸውን ገልጸው፤ አሁን ላይ ከኢትዮጵያ አልፎ የአፍሪካ አገራትን ማገልገል የሚያስችል ሥራ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል።
ተቋሙ መጀመሪያ ላይ የሥጋ ደዌ በሽታን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የተመሰረተ ቢሆንም፣ አሁን ላይ መድኃኒት የተለማመደ የቲቢ በሽታን፣ የወባ በሽታንና ሌሎች በርካታ የምርምር ሥራዎችን እያከናወነ ይገኛል።
ከምርምር በተጨማሪ በአገር ውስጥ የሚመረቱ መድኃኒቶች ጥራታቸውን የጠበቁ እንዲሆኑ ለማድረግ በምርመራ የመለየት ሥራ መከናወኑን ተናግረዋል።
የምርምር ማዕከሉ 40 ላቦራቶሪዎችን፣ የላቁ የጂኖሚክስ (genomics) እና የባዮኢንፎርማቲክስ (bioinformatics) ክፍሎችን፣ እንዲሁም በሀገር ውስጥ የሚመረቱ መድኃኒቶችን ጥራትና ብቃት የሚያረጋግጥ የባዮኢኩዊቫለንስ (bioequivalence) ማዕከልን አካትቷል።
በኢትዮጵያ እና በመላው አፍሪካ ለሳይንስ ሥነ ምሕዳር መስፋፋትና አቅም ግንባታ አዲስ መለኪያ ያስቀመጠው ተቋም ለሥልጠና እና ለምርምር የተመደቡ ቦታዎችን መያዙ ተገልጿል።