ቀጥታ፡

በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ተወዳዳሪ ትውልድ ለማፍራት የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረዋል

ድሬደዋ፤ ሚያዚያ 24/2018(ኢዜአ)፦ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ተወዳዳሪ ትውልድ በመገንባት ዲጂታል ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን የድሬዳዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ተናገሩ።

በአስተዳደሩ ለሶስት ቀናት የተካሄደው የትምህርት ቤቶች የሳይንስና የቴክኖሎጂ የፈጠራ ውጤቶች አውደ ርዕይ ዛሬ ተጠናቋል።

የድሬደዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት ፤በአውደ ርዕዩ  ላይ የቀረቡት  የፈጠራ ውጤቶች ዲጂታል ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግ የተጀመሩ አበረታች ጉዞዎችን ለማሳካት የጎለ አስተዋጽኦ ይኖራቸዋል ብለዋል።

በትምህርት ቤቶች የሳይንስና ቴክኖሎጂ ክህሎትና ጥበብ ያላቸውን ታዳጊ ተማሪዎችን ለማፍራት የሚከናወኑ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል።

በአውደ ርዕዩ የቀረቡ ችግር ፈቺ የሳይንስና የቴክኖሎጂ የፈጠራ ውጤቶች ጥቅም ላይ እንዲውሉ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር በቅንጅት ይሰራል ብለዋል።

የድሬዳዋ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሱልጣን አልይ በበኩላቸው፤ የሳይንስና የቴክኖሎጂ ዕውቀት፣ ክህሎትና ጥበብ የተላበሱ ታዳጊዎችን ለማፍራት የተጀመሩ ጥረቶች ፍሬያማ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናግረዋል።

በአውደ ርዕዩ በየዘርፉ የቀረቡ የቴክኖሎጂ የፈጠራ ውጤቶች የዚሁ መገለጫ መሆናቸውን በመግለፅ ።

በቀጣይም የፈጠራና የምርምር ስራዎችን በጥራት፣ በስፋት እና በተሻለ ከፍታ ለማሳደግ ከድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ እና ከድሬዳዋ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ምሁራን ጋር በቅንጅት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል ።

የድሬደዋ ዩኒቨርሲቲ የዘርፉ ምሁራን የፈጠራ ውጤቶቹን በመገምገም በየዘርፉ የተሻሉትን የፈጠራ ውጤቶች ደረጃ መለየቻቸውም ታውቋል።

በአውደ ርዕዩ ላይ በድሬደዋ አስተዳደር የሚገኙ የ1ኛ እና 2ተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች የሳይንስና የቴክኖሎጂ የፈጠራ ውጤቶች ናቸው የቀረቡት።

በአውደ ርዕዩ በየዘርፉ የተሻለ የፈጠራ ሃሳቦችን እና ውጤቶችን ይዘው ለቀረቡት ተማሪዎች ሽልማት ተሰጥቷል።

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም