ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በምርምር በማዳበር የመድኃኒት አቅርቦት ችግሮችን ለመፍታት እየተሠራ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በምርምር በማዳበር የመድኃኒት አቅርቦት ችግሮችን ለመፍታት እየተሠራ ነው
ደብረ ብርሃን፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፡- ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በምርምር በማዳበር የሀገር ውስጥ የመድኃኒት አቅርቦትን ለማሳደግ እየሠራ መሆኑን ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ።
ዩኒቨርሲቲው 5ኛውን ሀገር አቀፍ የጤና ምርምር ሲምፖዚየም አካሂዷል።
በዩኒቨርሲቲው የአሥራት ወልደየስ ጤና ሳይንስ ካምፓስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዶክተር ቴዎድሮስ ክፍለዮሐንስ በዚሁ ወቅት፤ ዩኒቨርሲቲው ሀገር በቀል ዕውቀቶች ላይ ተግባር ተኮር ምርም እያደረገ መሆኑን አስረድተዋል።
በአንኮበር የዕጽዋት የምርምር ጣቢያ በማቋቋም የመድኃኒት አቅርቦትና ሌሎች ዘርፎች ላይ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችል ሥራ እየሠራ መሆኑን አስታውቀዋል።
በጣቢያው ዕጽዋት ለመድኃኒት ቅመማና ክትባት ጥቅም ላይ የሚውሉበትን ዐቅም ለመፍጠር ከአርማወር ሐሰን የምርምር ኢንስቲትዩትና ሌሎች ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር በቅንጅት እየተሠራ ነው ብለዋል።
ዩኒቨርሲቲው በምርምር የተገኙ ውጤቶችን በማዳበር ወደ ተግባር የሚሸጋገሩበትን ሂደት ለማሳካት እየሠራ መሆኑን አንስተዋል።
በአርማወር ሐሰን የምርምር ኢንስቲትዩት የዕውቀት አስተዳደርና ሥርፀት ዳይሬክተር ዶክተር አክሊሉ ዓለሙ በበኩላቸው፤ ተቋሙ ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ በመድኃኒትና ክትባት ላይ በማተኮር እየሠራ ይገኛል።
በሀገር በቀል ዕውቀቶች ላይ የተመሰረተ የመድኃኒት አቅርቦት ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል በመሆኑ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር የጀመረው ቅንጅታዊ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
የጎንደር ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ ዶክተር እያሱ መስፍን ደግሞ፤ በዘርፉ የምርምር ኮንፈረንስ መዘጋጀቱ የዕውቅትና የልምድ ልውውጥ በማድረግ ችግር ፈች የምርምር ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥልሉ ያደርጋል ነው ያሉት።
ይህም በጤናው ዘርፍ እየተካሄደ የሚገኘውን በሽታን የመከላከልና አክሞ የማዳን አቅጣጫ በሳይንሳዊ ምርምር በማገዝ ውጤማ እንዲሆን የሚያደርግ መሆኑን አስረድተዋል።