የተቀናጀ የሚዲያ ሬጉላቶሪ እና አስተዳደር ስርዓት የቴክኖሎጂ ግልጽነት እና ተጠያቂነትን የሚያሰፍን ነው - ኢዜአ አማርኛ
የተቀናጀ የሚዲያ ሬጉላቶሪ እና አስተዳደር ስርዓት የቴክኖሎጂ ግልጽነት እና ተጠያቂነትን የሚያሰፍን ነው
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦የተቀናጀ የሚዲያ ሬጉላቶሪ እና አስተዳደር ስርዓት የቴክኖሎጂ ግልጽነት፣ ተጠያቂነትን የሚያሰፍን እና የዜጎችን ተሳትፎ የሚያጎለብት መሆኑን የብሔራዊ መረጃ እና ደህንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጄኔራል እና የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ቦርድ ሰብሳቢ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ገለጹ።
የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ከኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ጋር በመተባበር ያለማውን የተቀናጀ የሚዲያ ሪጉላቶሪ እና አስተዳደር ስርዓት ቴክኖሎጂ በይፋ ሥራ አስጀምሯል።
በመርሐ ግብሩ ላይ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እውነቴ አለነ፣ የብሔራዊ መረጃ እና ደህንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጄኔራል እና የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ቦርድ ሰብሳቢ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን፣ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር እናትዓለም መለሰ፣ ኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃይማኖት ዘለቀ፣ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር)፣ የመገናኛ ብዙኃን የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል።
የብሔራዊ መረጃ እና ደህንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጄኔራል እና የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ቦርድ ሰብሳቢ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የተቀናጀ የሚዲያ ሪጉላቶሪ እና አስተዳደር ስርዓት ስራን የሚያቀላጥፍ ነው።
ይህ ቴክኖሎጂ ግልጽነትንና ተጠያቂነትን የሚያሰፈን እንዲሁም የዜጎችን ተሳትፎ የሚያጎለብት መሆኑን ተናግረዋል።
በውሳኔ አሰጣጥ ላይም ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ጠቁመው፤ እንዲሁም ፈጣን ምላሽ መስጠት በማስቻል ለተቋሙ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ተናግረዋል።
ይህም ለዘርፉ እድገት የሚያበረክተው አስተዋጽኦ የጎላ መሆኑን ገልጸው፤ ቴክኖሎጂው ወደ ስራ እንዲገባ አስተዋጽኦ ያበረከቱ አካላትን አመስግነዋል።