ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አዲሱ አራዳ ፓርክን መርቀው ከፈቱ - ኢዜአ አማርኛ
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አዲሱ አራዳ ፓርክን መርቀው ከፈቱ
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ):- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አዲሱ አራዳ ፓርክን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል።
የአዲሱ አራዳ ፓርክ ታሪክ ጥልቅ ለውጥ የታየበትና በዛሬው ዕለት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ይፋ የተደረገ ታላቅ ፕሮጀክት መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ገልጿል።
ቀደም ሲል ተዘንግቶ፣ ለአደጋ የተጋለጡ ቤቶች የነበረው ይህ 40 ሄክታር መሬት፣ ዛሬ ተመልሶ ተገንብቶ ዘርፈ ብዙ አገልግሎት የሚሰጥ ቀዳሚ የከተማ መዳረሻ መሆኑን አመልክቷል።
ይህ ፕሮጀክት ፓርክ ብቻ ሳይሆን፤ የተቀናጀ መሠረተ ልማትና የመሬት አጠቃቀም ብቃት የታየበት ጥበብ መሆኑን አስታውቋል።
ከ700 በላይ ነባር ቤቶችንና ሕንፃዎችን በማደስ፣ ልማቱ ማኅበረሰቡን የሚያገል ሳይሆን የሚያቅፍ እንዲሆን መደረጉንም ጠቁሟል።
• ለምለም የከተማ መናፈሻ
ከጠቅላላው 40 ሄክታር መሬት ውስጥ 15 ሄክታሩ በአረንጓዴ የተሸፈነ ሲሆን፤ ይህም ለአዲስ አበባ መሀል እንደ መተንፈሻ ሆኖ ያገለግላል።
• ከተማን ማገናኘት
በዲዛይኑ ውስጥ ለእንቅስቃሴ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቷል፤ ይህም 5 ኪሎ ሜትር የአስፋልት መንገድ፣ 6 ኪሎ ሜትር የእግረኛ መሄጃ፣ እንዲሁም ለብስክሌትና ለሩጫ የሚሆኑ 5 ኪሎ ሜትር መንገዶችን ያካተተ ሲሆን፤
ይህም ጤናማና ንቁ የአኗኗር ዘይቤን ያበረታታል።
• የኢኮኖሚ ጥንካሬ
ፓርኩ ለንግድ እንቅስቃሴዎች ትልቅ ማዕከል ነው፤ ከፒያሳ ለተነሱ ነጋዴዎች ቅድሚያ የሚሰጡ 131 የንግድ ሱቆች፣ 7 ካፌዎችና ምግብ ቤቶች፣ ሱፐርማርኬትና የባንክ ቅርንጫፍ በመያዝ የኢኮኖሚ ዘላቂነትን ያረጋግጣል።
• ጤናና ባህል
ከአረንጓዴው ስፍራ በተጨማሪ ፓርኩ ዘመናዊ የስፖርት ማዘውተሪያ፣ ጂምናዚየም እና 7 አዳራሾችን ይዟል። ከዚህም ጎን ለጎን ለዓለም አቀፍ ደረጃ ጥበባትና ለማኅበራዊ ኩነቶች የተዘጋጁ 8 አደባባዮችና አምፊቲያትሮችን አካቷል።
• ቤተሰብና ዘመናዊነት
ሕፃናት የሚጫወቱባቸው 4 ስፍራዎችና ልዩ የሆነ 'ትንሿ ከተማ' (Miniature City) ተገንብቶላቸዋል።
በፈጠራ የታጀበ ባለብዙ ወለል ዲዛይን በመጠቀም በግርማ ሞገስ በተገነቡ አደባባዮች ሥር ደማቅ የንግድ ስፍራዎችን በማካተት የአራዳ ፓርክ ውድ የሆነውን የከተማ መሬት በእያንዳንዱ ስንዝር በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዲውል ማድረጉንም አመልክቷል።