ቀጥታ፡

የከተማ አስተዳደሩ ደንብ ማስከበር ባለስልጣን አሰራሩን በማዘመን በታላቅ የሽግግር ሂደት ላይ ይገኛል -ከንቲባ አዳነች አቤቤ

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ደንብ ማስከበር ባለስልጣን አሰራሩን በቴክኖሎጂ በማዘመን በታላቅ የሽግግር ሂደት ላይ እንደሚገኝ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።

የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የከተማ አስተዳደሩ ደንብ ማስከበር ባለስልጣን እያከናወነ የሚገኘውን የሪፎርም ሥራዎች ጎብኝተዋል።


 

ከንቲባዋ በጉብኝቱ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ ከተማ አስተዳደሩ ለተቋም ግንባታ የሰጠው ትኩረት ተጨባጭ ውጤት እያመጣ ነው ብለዋል።

ተቋማት ቀጣይነት ያለው ሥራ እንዲሰሩና የአገልግሎት አሰጣጣቸውም ዘላቂ እንዲሆን የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም የደንብ ማስከበር ባለስልጣን ትልቅ ማሣያ ነው ብለዋል።

ተቋሙ ከቅጣት ይልቅ ለህብረተሰቡ ግንዛቤ መስጠት ላይ እየሰራ መሆኑን አብራርተው፤ የደንብ ጥሰት ተፈጽሞ ሲገኝ ብቻ ተግባራዊ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

ባለስልጣኑ በቴክኖሎጂ ራሱን በማዘመንና በመረጃ ላይ በመመስረት ሕግና ሥርዓትን ወደ ማስከበር መሸጋገሩን ተናግረዋል።

በአሁኑ ወቅት ባለስልጣኑ ወረቀት አልባ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም የከተማዋ የስማርት ሲቲ ግንባታ አንዱ አካል መሆኑን ገልጸዋል።

አሰራሩን በሞባይል መተግበሪያም ጭምር በመስጠት ቀልጣፋ አገልግሎት ተደራሽ ማድረግ መጀመሩንም ተናግረዋል።


 

ማህብረሰቡ የደንብ ጥሰት ሲፈጸም ካለበት ቦታ ሆኖ ጥቆማ የሚሰጥበት ዘመናዊ አሰራር መዘርጋቱንም ጠቅሰዋል።

የደንብ ማስከበር ባለስልጣን አሰራሩን በማዘመን በታላቅ የሽግግር ሂደት ላይ እንደሚገኝም አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም