በብሔረሰብ አስተዳደሩ በመጪው መኸር ወቅት ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል - ኢዜአ አማርኛ
በብሔረሰብ አስተዳደሩ በመጪው መኸር ወቅት ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
ሰቆጣ ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር በ2018/19 የመኸር ወቅት ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን ለመቻል የተያዘውን ግብ ለማሳካት ትኩረት መደረጉ ተገለጸ።
መምሪያው የ2018/19 የመኸር እርሻ የንቅናቄ መድረክ በሰቆጣ ከተማ አካሄዷል።
የብሔረሰብ አስተዳደሩ ምክትል አስተዳዳሪና የኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ሃላፊ አቶ ሹመት ጥላሁን እንደገለጹት፤ ምርታማነትን ለማሳደግ የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችንና አሰራሮችን ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ነው።
አስተዳደሩ ዝናብ አጠር በመሆኑ አካባቢውን መሰረት ያደረገ የሰብል ልማት ለማካሄድ ከምርምር ተቋማት፣ ከአርሶ አደሩና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በተለይም የሰብል ምርታማነትን በየደረጃው በማሳደግ አርሶ አደሩን ከተረጂነት ለማላቀቅ ከላይ እስከ ታች ያለው አመራርና ባለሙያ ርብርብ ማድረግ እንዳለበትም አሳስበዋል።
የብሔረሰብ አስተዳደሩ ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አዲስ ወልዴ በበኩላቸው፤ በመጪው የመኸር ወቅት 120 ሺህ 638 ሄክታር መሬትን በዘር በመሸፈን 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ታቅዷል።
የታቀደውን ምርታማነት ለማሳካትም 44 ሺህ ኩንታል ሰው ሰራሽ ማዳበሪያና 6 ሺህ ኩንታል ምርጥ ዘር በማቅረብ እየተሰራጨ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
በምርት ዘመኑ የኩታ ገጠም አስተራረስንና የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም አርሶ አደሩን በምግብ ራሱን ለማስቻል የተያዘውን ግብ ለማሳካት እንደሚሰራም ገልጸዋል።
ስነ-ምህዳርን መሰረት ያደረጉና የተሻሻሉ አምስት ዓይነት የሰብል ዝርያዎችን ለማቅረብ ዝግጅት ተደርጓል ያሉት ደግሞ የሰቆጣ ዝናብ አጠር ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር አዳነ ባህሩ (ዶ/ር) ናቸው።
ማዕከሉ በምርት ዘመኑ በ80 ሄክታር መሬት ላይ የተሻሻሉ ዝርያዎችን የማባዛት ስራ እንደሚሰራ ጠቁመው በተጨማሪም ከ300 በላይ አርሶ አደሮች ማሳ ላይ የተሻሻሉ ዝርያ ያላቸው ሰብሎች ይለማሉ ብለዋል።
የዝቋላ ወረዳ ግብርና ፅህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ተሾመ ስመኝ በበኩላቸው፤ በመጪው ክረምት ለአካባቢው ተስማሚ የሆኑ የእንቁ፣ የዳጉሳና የማሾ ሰብሎችን በኩታ ገጠም ለማልማት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በንቅናቄ መድረኩ ላይ የብሔረሰብ አስተዳደሩ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣ የግብርና ባለሙያዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።