ቀጥታ፡

የመንግስት ሰራተኞች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸው በቴክኖሎጂ መስክ የመወዳደር አቅማቸውን ለማሳደግ አስችሏል

ገንዳውኃ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸው በቴክኖሎጂ መስክ አቅማቸውን በማሳደግ ተወዳዳሪነታቸው እንዲጨምር ማድረጉን በምዕራብ ጎንደር ዞን የሚገኙ የመንግስት ሰራተኞች ገለጹ። 

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ኢንሼቲቭ በመላው ሀገሪቷ የተጀመረው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በቴክኖሎጂ የበቃና ተወዳዳሪ የሰው ሀይልን ለማፍራት አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል።

5 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን ተጠቃሚ ለማድረግ ያለመው ሀገር አቀፍ ስልጠና ዲጂታል ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግም አበርክቶው የላቀ ነው።

ስልጠናው ፕሮግራሚንግ፣ በዳታ ሳይንስ፣ በአንድሮይድና በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ  መስኮች ዜጎች  ባሉበት ቦታ በበይነ-መረብ የሚከታተሉት  ነው።

በምዕራብ ጎንደር ዞን የመንግስት ኮሙኒኬሽን ባለሙያ የሆኑት አቶ ብሩክ ወርቄ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው በመሆኑ  ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል ነው። 

ስልጠናው የቴክኖሎጂ እውቀትንና ክህሎትን በማሳደግ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ይበልጥ ቀልጣፋና ውጤታማ ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን በተግባር አረጋግጠናል ነው ያሉት።

​​በዞኑ የመተማ ወረዳ አስተዳደር ሰራተኛ የሆኑት ወይዘሮ ሳራ ወንድሙ በበኩላቸው፤ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ዓለም ካለበት የስልጣኔ ደረጃ እኩል ለመራመድ የሚያስችል ነው ብለዋል። 

"አለም በቴክኖሎጂ እየተመራች ባለችበት በዚህ ወቅት፣ እኛም እንደ አንድ የመንግስት ሰራተኛ ራሳችንን ማዘመንና ማብቃት ይጠበቅብናል" ነው ያሉት።

ባገኙት ስልጠና ተጠቅመውም መረጃዎችን በዲጂታል ዘዴ በመሰብሰብ፣ በማቀናበርና ለተገልጋዩ ህብረተሰብ ቀልጣፋ ምላሽ ከመስጠት አንፃር አዲስ እይታ የፈጠረላቸው መሆኑን ተናግረዋል። 

​በዞኑ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቡድን መሪ አቶ ስሜነው ተላከ ፤ ስልጠናው የኮምፒውተር ፕሮግራሚንግና የዳታ አያያዝ ተግባራቸውን ለማቅለል እንዳስቻላቸው አስረድተዋል። 

ስልጠናው የላቀ ቅልጥፍና እና ጥራት ያለው አገልግሎት ለመስጠት ከማስቻሉም በላይ አለምአቀፍ እውቅና ያለው የምስክር ወረቀት በማግኘታቸው ተወዳዳሪነታቸው ለማሳደግ አስችሎናል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም