ቀጥታ፡

የመስሪያ ቦታና የመሰረተ ልማት አቅርቦት መኖሩ በተሰማራንበት ዘርፍ ውጤታማ አድርጎናል- አምራች ኢንዱስትሪዎች

ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦መንግስት ባደረገላቸው የመስሪያ ቦታና የተሳለጠ የመሰረተ ልማት አቅርቦት በተሰማሩበት መስክ ውጤታማ መሆናቸውን አምራች ኢንዱስትሪዎች ገለጹ፡፡

ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ350 ሚሊዮን ዶላር በላይ ተኪና የወጪ ምርት በክልሉ በሚገኙ አምራች ኢንዱስትሪዎች በኩል መመረቱን የክልሉ ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ገልጿል፡፡

የአምራች ኢንዱስትሪዎቹ የስራ ኃላፊዎች ለኢዜአ እንደገለፁት፤ መንግስት የመስሪያ ቦታና የተሳለጠ የመሰረተ ልማት አቅርቦት እንዲኖር ማድረጉ  በተሰማሩበት ዘርፍ ውጤታማ እንዲሆኑ እያደረገ ነው።

በሀዋሳ ከተማ በፎምና በቴራዞ ምርት የተሰማሩት አምራች ኢንዱስትሪ ስራ አስኪያጆች አቶ ዘሪሁን ሀይለማሪያም እና አቶ አዲስ አበበ፤ መንግስት የመስሪያ ቦታ፣የኃይልና ሌሎች አቅርቦቶች በማመቻቸቱ በአጭር ጊዜ ውጤታማ እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡

በአንድ ላይ 230 ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል እንደፈጠሩ የሚገልጹት አምራች ኢንዱስትሪዎቹ ከውጭ የሚገባውን ምርት በመተካት ረገድ ውጤታማ ስራ እየሰሩ መሆኑን አመልክተዋል።

የኩል ፕላስቲክ ሪሳይክሊንግ ኢንተርፕራይዝ ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ ሰላማዊት ቶማስ በበኩላቸው፤ መንግስት እያደረገ ያለው ድጋፍ ተኪ ምርት በማምረት ስኬታማ እንዲሆኑ ማድረጉን አስረድተዋል፡፡

በአምራች ኢንዱስትሪዎቹ የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች መካከል ወጣት ሰለሞን ጋሻው በተፈጠረለት የስራ ዕድል ቤተሰቡን እያስተዳደረ እንደሚገኝ ነው የገለጸው።

ባገኘው የስራ ዕድልም ከሚያገኘው ገቢ በተጨማሪ የዕውቀት ሽግግር ዕድል ማግኘቱንም ተናግሯል።

የሲዳማ ክልል የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አሻግሬ ጀንበሬ ለኢዜአ እንደገለጹት ፤በክልሉ በወጪና ተኪ ምርቶች ላይ የተሰማሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅምን ለማጎልበት የሚያስችሉ ስራዎች በተቀናጀ መንገድ እየተከናወኑ ነው፡፡

በተለይም የኤሌክትሪክ ኃይል፣ ጥሬ ዕቃ፣ የተማረ የሰው ኃይልና ሌሎች አቅርቦቶችን በማመቻቸትና በምርታማነት ሂደት የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለቅሞ ለመፍታት የተወሰዱ እርምጃዎች ውጤት ማምጣታቸውን ጠቅሰዋል፡፡

በዚህም በክልሉ የኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም ከ65 በመቶ በላይ ዕድገት ማሳየቱን ጠቁመው ባለፉት ዘጠኝ ወራት ወደ ውጭ ከተላኩ ምርቶች ከ120 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ ተገኝቷል ነው ያሉት።

በዚህም ከ230 ሚሊዮን ዶላር በላይ የሚያወጣ ምርት መተካት መቻሉን ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም