መንግሥት የዜጎችን የኑሮ ጫና ለመቀነስ በርካታ ቢሊዮን ብሮችን በመመደብ እና አመራጮችን ሁሉ አሟጦ በመጠቀም የነዳጅ አቅርቦትን አስቀጥሏል - ኢዜአ አማርኛ
መንግሥት የዜጎችን የኑሮ ጫና ለመቀነስ በርካታ ቢሊዮን ብሮችን በመመደብ እና አመራጮችን ሁሉ አሟጦ በመጠቀም የነዳጅ አቅርቦትን አስቀጥሏል
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ መንግሥት የዜጎችን የኑሮ ጫና ለመቀነስ በርካታ ቢሊዮን ብሮችን በመመደብ እና አማራጮችን ሁሉ አሟጦ በመጠቀም የነዳጅ አቅርቦትን ማስቀጠሉን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት አስታወቀ።
መንግሥት በመሠረታዊ ፍላጎቶቿ በራሷ የምታሟላ ሉዓላዊ ሀገር ለመፍጠር ፖሊሲ ቀርጾ እየሠራ ይገኛል። በተለይም ከነዳጅ ጥገኝነት ለመላቀቅ ቀድሞ ወደ ሥራ መግባቱ፣ በሀገር ላይ ይደርስ የነበረን የከፋ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ከሌሎች ሀገራት አንጻር በከፍተኛ ደረጃ ማስቀረት እንደቻለ ገልጿል።
ምንም እንኳ ሙሉ ለሙሉ ከነዳጅ ጥገኝነት ለመላቀቅ ገና ሰፊ የመንግሥት እና የግሉ ዘርፍ ጥረት ቢጠይቅም፣ ባለፉት ስምንት ዓመታት በታዳሽ የኃይል ዘርፍ አቅርቦት ላይ የተሠራው ሥራ አሁን ያለውን ቀውስ ለመቋቋም በእጅጉ ማገዙን አመልክቷል።
የኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ሙሉ በሙሉ ከታዳሽ የኃይል ምንጮች ማለትም ከውኃ፣ ከነፋስ እና ከፀሐይ የሚገኝ ሲሆን፤ በቀጣይም ከጂኦተርማል እና ከኑክሊየር ኃይል በማመንጨት የሀገሪቱን ፍላጎት በአስተማማኝ ደረጃ ለማሟላት እየተሠራ ይገኛልም ነው ያለው አገልግሎቱ።
የኃይል ምንጮችን ታዳሽ ማድረግ መቻሉ፣ አሁን ካጋጠመው ዓለም አቀፍ የነዳጅ እጥረትና የዋጋ መናር ጋር ተያይዞ በሀገሪቱ አምራች ኢንዱስትሪዎች ላይ ሊከሰት ይችል የነበረን ጫና ማስቀረት ማስቻሉን ገልጿል።
መንግሥት ላለፉት ዓመታት ዜጎች የታዳሽ ኃይል አማራጮችን እንዲጠቀሙ የተለያዩ የማበረታቻ ሥርዓቶችን ተግባራዊ አድርጓል።
በዚህም የመንግሥትን አቅጣጫ በመቀበል የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን መጠቀም የጀመሩ ዜጎች አሁን ላይ የችግሩ ሰለባ አለመሆናቸውን መረጃው አመላክቷል።
ይህም ለዘገዩት ትምህርት የሚሰጥ ሲሆን፣ ለመንግሥት ደግሞ ለሚከተለው የፖሊሲ አቅጣጫ ትክክለኛነት በራስ መተማመን የሚፈጥር እንደሆነም ተነስቷል።
በአሁኑ ወቅት ከ140 ሺህ ያላነሱ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የሚገኙ ሲሆን፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ይህንን መጠን በብዙ እጥፍ ለማሳደግ ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን አገልግሎቱ ጠቁሟል።
መንግሥት የኃይል ሉዓላዊነትን በታዳሽ የኃይል ምንጮች ላይ ተመሥርቶ ለማረጋገጥ ጥረት እያደረገ ነው።
የታላቁ ሕዳሴ ግድብ መጠናቀቅ የኢትዮጵያን የኃይል አቅርቦት በከፍተኛ ደረጃ ሲያሳድገው፣ የነፋስ ኃይል ማመንጫዎችም በየጊዜው እየተመረቁ ወደ ሥራ እየገቡ ይገኛሉ። በአፍሪካ ግዙፍ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ሶላር ፓኔሎችን የማምረት አቅም የተፈጠረ ሲሆን፣ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎም እየተበረታታ እንደሚገኝም ተነስቷል።
በተጨማሪም የነዳጅ ማጣሪያ እና የተፈጥሮ ጋዝ ማምረቻ ፋብሪካዎች ግንባታ እየተፋጠነ መሆኑ ተጠቁሟል።
በእነዚህ ሁሉ ጥረቶች መካከል አሁን ያጋጠመው ዓለም አቀፍ ቀውስ በዜጎች ላይ የከፋ ጉዳት እንዳያደርስ ለመከላከል፣ መንግሥት ቀደም ሲል ሲደጉም ከነበረው በተጨማሪ በየወሩ 20 ቢሊዮን ብር በመደጎም እና የተለያዩ አማራጮችን በመጠቀም የነዳጅ አቅርቦትን እያስቀጠለ እንደሚገኝ አገልግሎቱ አስታውቋል።
መንግሥት በአረንጓዴ የኢኮኖሚ ፖሊሲ አቅጣጫ አማካኝነት ችግሩን በዘላቂነት ከሕዝቡ ጋር እንደሚሻገረው እና የመውጫ በሩም ከቅርብ ርቀት ይታያል ሲል አገልግሎቱ በመረጃው አመላክቷል።