መንግስት የናፍጣ የአቅርቦት መጠን ከዛሬ ጀምሮ ከመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በፊት ወደነበረበት እንዲመለስ ወሰነ - ኢዜአ አማርኛ
መንግስት የናፍጣ የአቅርቦት መጠን ከዛሬ ጀምሮ ከመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በፊት ወደነበረበት እንዲመለስ ወሰነ
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ መንግስት የናፍጣ ነዳጅ የአቅርቦት መጠን ከዛሬ ጀምሮ ከመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በፊት ወደነበረበት እንዲመለስ መወሰኑን የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ገለጹ፡፡
የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ወቅታዊ የዓለም የነዳጅ ሁኔታን በማስመልከት ለመገናኛ ብዙኅን ማብራሪያ ሰጥተዋል።
የገንዘብ ሚኒስትሩ በመግለጫቸው፤ የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት በዓለም የነዳጅ አቅርቦትና ዋጋ ላይ ከፍተኛ ጫና መፍጠሩን አብራርተዋል።
በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ነዳጅ ሙሉ በሙሉ ከውጭ የሚያስገቡ ሀገራት በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚፈተኑ ገልጸዋል፡፡
መንግሥት የተከሰተው ዓለም አቀፍ የነዳጅ አቅርቦት ችግር በዜጎች ኑሮ ላይ የጎላ ጫና እንዳይፈጥር ተቋማትን በማቀናጀትና የ24 ሰዓት የመከታተያ ክፍል በማቋቋም ክትትል ሲያደርግ መቆየቱን አስታውሰዋል፡፡
በዚህም መንግስት በአጣዳፊ ግዥ የቤንዚንና የአውሮፕላን ነዳጅ በመግዛት ችግሩን መቋቋም የሚያስችል አስተማማኝ ሥራ መስራቱን ተናግረዋል፡፡
መንግሥት ከጦርነቱ በፊት በቀን 9 ሚሊዮን ሊትር ናፍጣ ያቀርብ እንደነበር አስረድተዋል።
ከጦርነቱ በኋላም የነዳጅ ዲፖዎችን ለመሙላትና የኢኮኖሚ ቁጠባን ለማረጋገጥ አቅርቦቱ በቀን ወደ 4 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሊትር ዝቅ እንዲል ማድረጉን ተናግረዋል።
ይሁን እንጂ ወቅቱ የግብርና ግብዓትና ሥራዎችን በከፍተኛ ሁኔታ ማከናወን፣ የውጭ ንግድ ማቀላጠፍ፣ ነዳጅን እንደ ግብዓት የሚጠቀሙ አምራች ዘርፎች እጥረት እንዳይገጥማቸው የተለያዩ ፕሮጀክቶች ጫና እንዳይፈጠርባቸው በማሰብ አቅርቦቱ እንዲሻሻል ተደርጓል ብለዋል።
በመሆኑም ከዛሬ ጀምሮ በሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የናፍጣ አቅርቦት ከጦርነቱ በፊት ወደ ነበረበት በቀን ዘጠኝ ሚሊዮን ሊትር እንዲመለስ መወሰኑን ገልጸዋል።
መንግሥት ጦርነቱን ተከትሎ በወር እስከ 20 ቢሊዮን ብር ተጨማሪ ድጎማ እያደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ አጠቃላይ የድጎማ ክምችቱ 300 ቢሊዮን ብር መድረሱን አስታውቀዋል።
የመሰረታዊ የሸቀጥ አቅርቦትን አስተማማኝ ለማድረግም ከፍተኛ ሥራ በመስራት የዜጎችን የኑሮ ጫና እየፈታ ቀጣይነት ያለው ፈጣን ዕድገት ማስመዝገብ እየተቻለ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
የዓለም የነዳጅ አቅርቦት ሰንሰለት በከፍተኛ ሁኔታ በተጎዳበት ወቅትም በልዩ ግዥ፣ በከፍተኛ ድጎማና በከፍተኛ ዋጋ እየቀረበ መሆኑን ተናግረዋል።
መንግሥት ነዳጅ በልዩ ግዥና በከፍተኛ ወጭ እያቀረበ ባለበት ወቅት አሻጥር በመፍጠር በሕገ-ወጥ ሥራ ላይ የሚሰማሩ አካላትን መቆጣጠር እንደሚገባም አሳስበዋል።
በመሆኑም ህብረተሰቡ ከጸጥታና ሌሎች የመንግስት ተቋማት ጋር በመተባበር በሕገ-ወጥ ድርጊት ላይ የሚሳተፉ አካላትን በመቆጣጠር ትብብር እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።