ቀጥታ፡

የትራንስፖርት አገልግሎትን ከነዳጅ ጥገኝነት ለማላቀቅ ተግባራዊ የተደረጉ ስልቶች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ ነው 

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦የትራንስፖርት አገልግሎትን ከነዳጅ ጥገኝነት ለማላቀቅ ተግባራዊ የተደረጉ ስልቶች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር አስታወቀ። 

የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ በረኦ ሀሰን፤ የቻይና ኮሙኒኬሽንስ ኮንስትራክሽን ኩባንያ (CCCC) የገዛቸውን 92 ዘመናዊ የኤሌክትሪክ የጭነት ተሽከርካሪዎች በእንዶዴ ባቡር ጣቢያ በመገኘት ሥራ አስጀምረዋል፡፡


 

እነዚህ ተሽከርካሪዎች ሙሉ በሙሉ በኤሌክትሪክ የሚሰሩ በመሆናቸው፣ መንግሥት ከያዘው የአረንጓዴ ትራንስፖርት ስትራቴጂ ጋር የተጣጣሙ መሆናቸው ተገልጿል። 

ተሽከርካሪዎቹ ለቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ግንባታ አገልግሎት የሚውሉ መሆኑም በዚሁ ወቅት ተጠቁሟል፡፡ 

ሚኒስትር ዴኤታው በረኦ ሀሰን በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ መንግሥት የትራንስፖርት ዘርፉን ከነዳጅ ጥገኝነት ለማላቀቅ ውጤታማ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። 

በተለይም በሀገሪቱ እየተገነቡ ባሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ላይ የሚሰማሩ ተሽከርካሪዎችና መሣሪያዎች ከነዳጅ ጥገኝነት ለማላቀቅ ተግባራዊ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡

በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች በስፋት ጥቅም ላይ እንዲውሉ በተዘረጋው አሠራር፣ በአሁኑ ወቅት 17 ድርጅቶች በሀገር ውስጥ የመገጣጠም ሥራ መጀመራቸውን አመልክተዋል። 

እነዚህ ድርጅቶች ከሁለት እግር ተሽከርካሪዎች ጀምሮ እስከ 400 ኩንታል የመሸከም አቅም ያላቸውን የጭነት ተሽከርካሪዎች እየገጣጠሙ እንደሚገኙም አብራርተዋል።

በተጨማሪም የመንግሥት ተቋማትና ዩኒቨርሲቲዎች የሚገዟቸው ተሽከርካሪዎች እንዲሁም የከተማ የሕዝብ ትራንስፖርት ባሶች ሙሉ በሙሉ የኤሌክትሪክ እንዲሆኑ መወሰኑን ጠቅሰዋል። 

ዘርፉን ይበልጥ ለማበረታታትም ነዳጅ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችን ወደ ኤሌክትሪክ ለመቀየር የሚያስፈልጉ የቴክኖሎጂ ግብዓቶች ከቀረጥ ነፃ እንዲገቡ መደረጉን አስታውሰዋል።

በዘርፉ የግሉን ተሳትፎ ይበልጥ ማሳደግ የሚያስችሉና የሚያበረታቱ አሰራሮች እየተዘረጉ መሆኑን ገልጸው፤ በዚህም ተጨባጭ ውጤቶች እየመጡ መሆኑን ተናግረዋል።

አሁን በቻይናው ተቋራጭ ተገዝተው የገቡት የሲኖ ብራንድ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ከፍተኛ ጥራት ያላቸውና ለሀገሪቱ የአረንጓዴ ልማት ጉዞ ትልቅ አስተዋጽኦ የሚኖራቸው መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም