በድሬዳዋ በግማሽ ቢሊዮን ብር በሚጠጋ ወጪ በተገነቡ ሞዴል ሼዶች አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች የማምረት ስራ ጀምረዋል - ኢዜአ አማርኛ
በድሬዳዋ በግማሽ ቢሊዮን ብር በሚጠጋ ወጪ በተገነቡ ሞዴል ሼዶች አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች የማምረት ስራ ጀምረዋል
ድሬዳዋ፣ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ) በድሬዳዋ በግማሽ ቢሊዮን ብር በሚጠጋ በጀት በተገነቡ ሞዴል ሼዶች አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች የማምረት ስራ መጀመራቸውን የአስተዳደሩ የኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ።
እነዚሁ የአነስተኛና መካከለኛ የኢንዱስትሪ ሼዶች ወደ ማምረት ስራ መግባታቸው፣ የከተማዋን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ከማነቃቃት ባለፈ ለሀገሪቱ የኢንዱስትሪ ሽግግር ትልቅ ፋይዳ እንዳላቸውም ተመላክቷል።
በድሬደዋ አስተዳደር በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪዎች ምርትና ምርታማነት መጎልበት እየተከናወኑ የሚገኙት ሁሉንአቀፍ የድጋፍና ክትትል ተግባራት መሠረታዊ ለውጥ በማስገኘት ላይ ናቸው።
ጎን ለጎንም አስተዳደሩ በሀገር አቀፍ ደረጃ በሞዴልነት እየተጠቀሱ የሚገኙ 18 ዘመናዊ የማምረቻ ሼዶችን በመገንባት ለአነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች በማስተላለፍ ውጤታማ ስራ እያከናወነ ይገኛል።
የአስተዳደሩ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ኡስማን አህመድ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት ከ482 ሚሊዮን ብር በላይ በሚሆን ወጪ 18 ዘመናዊ ሼዶችን ገንብቶ ለአነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች በማስተላለፍ ምርትና ምርታማነት እንዲጨመር አድርጓል።
ከ600 እስከ 1ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የተገነቡት እነዚሁ ሞዴል ሼዶችን የተረከቡ አነስተኛና መካከለኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች አብዛኛዎቹ ወደ ማምረት የተሸጋገሩ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል።
ጥቂቶቹ ደግሞ የማምረቻ ማሽኖችን ከውጪ በማስገንባት ላይ እንደሚገኙ በማከል።
ከድሬዳዋ ኢንዱስትሪ መንደር ጎን ለተገነቡት ሼዶች ሁሉም መሠረተ ልማቶች ከማሟላት ባሻገር አካባቢው ተለይቶ እንዲታጠር መደረጉን አንስተዋል።
ከሼዶቹ በተጨማሪ በጨርቃ ጨርቅ እና አልባሳት ዘርፍ ለተሰማሩ አምራቾችም ባለ አራት ወለል ህንፃ ተገንብቶ ወደ ስራ መገባቱን አስታውሰዋል።
እንደ አቶ ኡስማን ገለፃ አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎቹ ከ2ሺህ 800 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የስራ እድል ከመፍጠራቸው ባሻገር ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በጥራት እና በብዛት በማምረት የውጭ ምንዛሬ እያዳኑ ይገኛሉ።
በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት በአስተዳደሩ 490 የአነስተኛና መካከለኛ አዳዲስ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ወደ ስራ በማስገባትና ነባሮችን በማጠናከር የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማላቅ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝም አቶ ኡስማን አስታውቀዋል።
"ድሬ ታምርት፤ ኢትዮጵያ ትበልፅግ" በሚል መሪ ቃል በድሬዳዋ የተዘጋጀው የአምራች ኢንዱስትሪዎች ኤክስፖ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት መካሄዱ ይታወሳል።