ቀጥታ፡

በአማራ ክልል የህዝቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በቅንጅት የሚተገበሩ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ

ባህር ዳር፤ ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ የህዝቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በመንግስትና በሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ትብብር የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ገለጹ።

የክልሉ ገንዘብ ቢሮ የመንግስትና የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ዓመታዊ የአጋርነት የምክክር መድረክ በባህር ዳር ከተማ ዛሬ መካሄድ ጀምሯል።


 

ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) በመድረኩ እንደገለጹት፤ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የሚጠበቅባቸውን የልማት አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ምቹ ፖሊሲና አሰራር ተቀርጾ ተግበራዊ ተደርጓል።

ድርጅቶቹ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ስራዎች፣ በዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታና በሰብዓዊ ድጋፍ እያበረከቱ ያለው አስተዋጽኦ የሚበረታታ መሆኑን ገልጸዋል።


 

ድርጅቶቹ ያላቸውን ልምድና ተሞክሮ ተጠቅመው የመንግስትን የልማት አቅጣጫ መሰረት በማድረግ በድህነት ቅነሳና የተለያዩ ችግሮችን በመፍታት የድርሻቸውን እየተወጡ መሆኑን ተናግረዋል።

የማህበረሰብ ድርጅቶቹ በሚያከናውኑት ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ላይ ተገቢውን ድጋፍና ጥበቃ እንደሚደረግም አመልክተዋል።


 

የክልሉ ገንዘብ ቢሮ ኃላፊ አቶ አታላይ ጥላሁን በበኩላቸው፤ በክልሉ በርካታ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በተለያዩ የልማት ዘርፎች እየተሳተፉ እንደሚገኙ ተናግረዋል።

ቢሮው የልማት አጋሮች የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡና የሚያጋጥሟቸውን የአሰራር ክፍተቶች እንዲሞላም የአዋጅና የመመሪያ ማሻሻያዎችን እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

የምክክር መደረኩ ዋና ዓላማም በመንግስትና በአጋር ድርጅቶች መካከል የአሰራር ግልጸኝነትና ተጠያቂነት በመፍጠር በቅንጅት ለመስራት ያለመ ነው ብለዋል።

በቢሮው የሲቪል ልማት ድርጅቶች ማስተባበሪያ ዳይሬክተር አቶ አዝመራው ተጫነ እንዳሉት፤ በክልሉ ያሉ 170 የማህበረሰብ ድርጅቶች ከ24 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት በመመደብ እየሰሩ ይገኛሉ።


 

በዚህም የክልሉን ማህበረሰብ የሚጠቅሙ የግብርና፣ የጤና፣ የትምህርት፣ የንጹህ መጠጥ ውሃና ሌሎች የልማት ዘርፎች ከ350 በላይ ፕሮጀክቶችን በማከናወን ላይ እንደሚገኙ አብራርተዋል።

ለሁለት ቀናት በሚቆየው የምክክርና የልማት ስራዎች ኤግዚቢሽን ማጠናቀቂያ ላይም ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ 25 ድርጅቶች ልዩ እውቅናና ሽልማት እንደሚበረከትላቸው ተመልክቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም