በሀረሪ ክልል በገጠር ኮሪደር ልማት ሁለተኛው ዙር ሞዴል የአርሶ አደሮች መንደር ግንባታ ተጀመረ - ኢዜአ አማርኛ
በሀረሪ ክልል በገጠር ኮሪደር ልማት ሁለተኛው ዙር ሞዴል የአርሶ አደሮች መንደር ግንባታ ተጀመረ
አዲስ አበባ ፤ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ) ፦ በሀረሪ ክልል በገጠር ኮሪደር ልማት ሁለተኛው ዙር ሞዴል የአርሶ አደሮች መንደር ግንባታ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ በተገኙበት ተጀምሯል።
ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ ሞዴል የአርሶ አደሮች የመኖሪያ መንደር ግንባታ ባስጀመሩበት ወቅት እንዳሉት የክልሉ መንግስት ከመቼውም ጊዜ በላቀ ሁኔታ የዜጎችን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል።
በኮሪደር ልማቱ ሀረር ከተማን ተምሳሌት እንድትሆን ያስቻሉ ውጤታማ ስራዎች እንደተከናወኑ ሁሉ ስኬቱን በገጠር ኮሪደር ልማትም በክልሉ የተለያዩ ወረዳዎች ለመድገም እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።
በክልሉ በተለያዩ ወረዳዎች የሚከናወኑ የገጠር ኮሪደር ልማት ስራዎች አስፈላጊው የመሰረተ ልማት እንዲሟላ ከማድረግ ባለፈ አርሶ አደሩ ዘመናዊና የተመቸ ኑሮ እንዲመራ ያስችላል ሲሉም ተናግረዋል።
ከዚህ ቀደምም በገጠር ኮሪደር ልማት የቤት ቁሳቁስ የተሟላላቸው ዘመናዊ የመኖሪያ ቤቶች ተገንብተው ለአርሶ አደሮች እንዲተላለፉ መደረጉን አንስተዋል።
በሁለተኛው ዙር ሞዴል የአርሶ አደሮች መንደር ፕሮጀክትም 250 ቤቶች እንደሚገነቡ ጠቁመዋል።
ሞዴል የአርሶ አደሮች መንደር ግንባታ አካባቢያዊ ሀብቶችን በመጠቀም እውን እንደሚደረግ ጠቁመው በየአካባቢው የሚገኙ አርሶ አደሮችም ለፕሮጀክቱ መሳካት እንደከዚህ ቀደሙ በቅንጅት እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል።
ርዕሰ መስተዳድሩ ከዚህ በተጨማሪም በክልሉ በከተማና በገጠር እየተከናወኑ የሚገኙ ስራዎችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።