በአዊ ብሔረሰብ አሥተዳደር ዞን በመጭው የምርት ዘመን ከ412 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በዘር ይሸፈናል - ኢዜአ አማርኛ
በአዊ ብሔረሰብ አሥተዳደር ዞን በመጭው የምርት ዘመን ከ412 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በዘር ይሸፈናል
ባህር ዳር፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- በአዊ ብሔረሰብ አሥተዳደር ዞን በመጭው የመኸር ወቅት 412 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በዘር ለመሸፈን እየተሠራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ።
በመምሪያው የሰብል ልማትና ጥበቃ ቡድን መሪ አንዱዓለም አያሌው ለኢዜአ እንዳሉት፤ ለመጭው የመኸር ወቅት 412 ሺህ 480 ሔክታር መሬት በዘር በመሸፈን ከ17 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ እየተሠራ ነው።
ከዚህ ውስጥም 70 በመቶው በኩታ ገጠም የሚለማ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅትም ከ85 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት ለ2ኛ ጊዜ ደጋግሞ በማረስ ለዘር ዝግጁ ተደርጓል ብለዋል።
ከሚያስፈልገው 840 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ እስካሁን ከ72 በመቶ በላይ የሚሆነውን በማስገባት ለአርሶ አደሩ እየተሰራጨ መሆኑን አረጋግጠዋል።
ከ5 ሺህ ኩንታል በላይ የበቆሎ ምርጥ ዘር ተሰራጨቷል ያሉት ቡድን መሪው፤ በመስመር መዝራትና ዘመናዊ ቴክኖሎጅዎችን መጠቀም ላይ በማተኮር እንደሚሰራም አስረድተዋል።
በየደረጃው ያለው የግብርና ባለሙያ እና አመራሩ አርሶ አደሩን በመደገፍና በማማከር የሚጠበቀውን የምርት እድገት ለማስመዝገብ በቁርጠኝነት እየሠራ መሆኑን ምአስገንዝበዋል።