ቀጥታ፡

በአማራ ክልል ከ22 ሚሊዮን በላይ የቡናና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል

ባህርዳር፤ ሚያዝያ 19/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በመጪው ክረምት ለሚካሄደው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ከ22 ሚሊዮን በላይ የቡናና የሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸው ተገለጸ።

‎በቢሮው የሆርቲካልቸር ባለሙያ አቶ አወቀ ዘላለም ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በክልሉ ተስማሚ ስነ-ምህዳርና የአየር ንብረት ያላቸውን አካባቢዎች በመለየት ቡናና ሌሎች ፍራፍሬዎችን በክላስተር የማልማት ስራ እየተካሄደ ነው።

‎በተያዘው በጋ ወቅትም ከፍተኛ ምርት የሚሰጡና በሽታን የሚቋቋሙ ከ22 ነጥብ አራት ሚሊዮን በላይ የቡናና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።


 

‎ለተከላ ከተዘጋጁት ችግኞች መካከል ወደ 12 ነጥብ 2 ሚሊዮን የሚጠጋው የቡና ችግኝ ሲሆን ቀሪው ደግሞ የቆላና የደጋ ፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን ተናግረዋል።

‎‎ክልሉን በቡናና ፍራፍሬ ልማት ሞዴል ለማድረግም ሽፋኑንና ምርታማነቱን በማሳደግ ላይ በማተኮር የአርሶ አደሩ ዘላቂ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።

‎‎‎ለመጪው ክረምት ለተከላ እየተዘጋጀ ያለው ችግኝም ከ32 ሺህ ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ የሚተከል መሆኑን አስረድተዋል።

‎‎በምዕራብ ጎጃም ዞን የጃቢ ጠህናን ወረዳ አርሶ አደር ተፈራ መለሰ ፤ ባለፉት ዓመታት በአንድ ሄክታር መሬት ላይ ቡናን የማልማት ስራ መስራታቸውን ጠቅሰዋል።


 

በመጪው የክረምት ወቅትም በተጨማሪ ሩብ ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝን በኩታ ገጠም ለመትከል አቅደው እየሰሩ መሆኑን አስረድተዋል።

‎‎የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በመትከል የተሻለ ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን የገለፁት ደግሞ የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ውበት ተስፌ ናቸው።

‎ባለፈው ዓመት የክረምት ወቅት ከተተከሉ ወደ 17 ነጥብ 7 ሚሊዮን የሚጠጋ ቁጥር ያላቸው የቡና፣ የቆላና ደጋ ፍራፍሬ ችግኞች 93 ነጥብ 5 በመቶው መጽደቁን የቢሮው መረጃ ያመለክታል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም