ተማሪዎች ችግር ፈቺ የፈጠራ ስራዎችን እንዲያፈልቁ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል - ኢዜአ አማርኛ
ተማሪዎች ችግር ፈቺ የፈጠራ ስራዎችን እንዲያፈልቁ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 17/2018 (ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ ከተማ ተማሪዎች ችግር ፈቺና ተወዳዳሪ የፈጠራ ስራዎችን እንዲያፈልቁ ምቹ ሁኔታ በመፍጠር ውጤታማ ስራዎች መሰራታቸውን የከተማው ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዘላለም ሙላቱ (ዶ/ር) ገለጹ።
ቢሮው “በሳይንስና ፈጠራ የተካነ ትውልድ ለተምሳሌታዊ ሀገር” በሚል መሪ ሐሳብ ለሁለት ቀናት ሲያካሂድ የቆየው 11ኛው የሳይንስና የፈጠራ ስራ አውደ ርዕይ ተጠናቋል።
በአውደ ርዕዩም በተማሪዎችና መምህራን የቀረቡ የፈጠራ ሀሳቦች ተወዳድረው የላቀ ውጤት ላመጡ ተሳታፊዎች የሽልማት አሰጣጥ ስነ-ስርዓት ተከናውኗል።
የቢሮው ኃላፊ ዘላለም ሙላቱ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ተማሪዎች ከቀለም ትምህርት ጎን ለጎን የፈጠራ ክህሎታቸውን አውጥተው እንዲጠቀሙ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል።
በየዓመቱ የሚዘጋጀው ይህ የሳይንስና የፈጠራ ስራ አውደ ርዕይም ተማሪዎችና መምህራን ስራዎቻቸውን እንዲያቀርቡና የልምድ ልውውጥ እንዲያደርጉ ትልቅ ዕድል የፈጠረ መሆኑን ገልፀዋል።
ውድድሩ ተማሪዎችን በምርምርና በስልጠና በማገዝ ብቁና ተወዳዳሪ ትውልድ ለመቅረፅ ያለመ መሆኑን የጠቀሱት ኃላፊው፤ ተማሪዎች በንድፈ ሀሳብ የተማሩትን በተግባር እንዲከውኑና ወደ ሳይንሳዊ ግኝት እንዲቀይሩ ትልቅ አቅም መፈጠሩን አስረድተዋል።
በዘንድሮው አውደ ርዕይ ላይ ወደ 3 ሺህ 7 መቶ የሚጠጉ የፈጠራ ስራዎች ለውድድር መቅረባቸውን ጠቅሰው ከእነዚህም ውስጥ ከፍተኛ ውጤት ላመጡ አሸናፊዎች የእውቅና ሽልማት ተበርክቷል ብለዋል።
መድረኩ ከውድድር ባለፈ ለብዙዎች የተሻለ ነገን በተስፋ ለመጠበቅ መሠረት የሚጥል መሆኑን ጠቁመው፣ ለዚህም ስኬት ከቅድመ ዝግጅት ጀምሮ በትኩረት ሲሰራ መቆየቱን ገልፀዋል።
ከአውደ ርዕዩ ተሳታፊዎች መካከል የኢትዮ-ጃፓን 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ ሃብታሙ ደምስ ፤ለእርሻ አገልግሎት የሚውልና በፀሐይ ሃይል የሚሰራ ትራክተር በመስራት በውድድሩ የ1ኛ ደረጃ አሸናፊ ሆኗል።
ተማሪ ሃብታሙ ፤ አርሶ አደሩ ከባህላዊ የእርሻ ዘዴ ተላቆ በቴክኖሎጂ ታግዞ እንዲያመርት ለማስቻል መሣሪያውን እንደሰራ ገልጿል።
በተመሳሳይ የቡርቃ ዋዮ ትምህርት ቤት ተማሪ ፌኔት በንቲ፤ በስዕልና ቅርፃቅርፅ የፈጠራ ስራ ተወዳድራ የ2ኛ ደረጃ አሸናፊ መሆን ችላለች።
ተሳታፊ ተማሪዎቹ እንደገለጹት፤ መሰል አውደ ርዕዮች ያላቸውን እምቅ አቅም አውጥተው እንዲጠቀሙና ከሌሎች ተማሪዎች ልምድ እንዲቀስሙ ትልቅ እገዛ እያደረገላቸው ይገኛል።