ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳር የቼክ ሪፐብሊክ ባለሃብቶችን ቀልብ እየሳቡ ነው

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳር የቼክ ሪፐብሊክ አልሚ ባለሃብቶችን ቀልብ እየሳቡ እንደሚገኝ የቼክ ሪፐብሊክ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ራዴክ ሩበሽ ገለጹ።

የኢትዮጵያ እና ቼክ ሪፐብሊክ ታሪካዊ ግንኙነትም በሁሉም መስክ የትብብር አድማሱን እያሰፋ እንደሚገኝም ተናግረዋል።

የኢትዮ-ቼክ ሪፐብሊክ የፖለቲካል ዲፕሎማቲክ ግንኙነት እ.አ.አ ከ1918 ጀምሮ በታሪካዊ ወዳጅነትና ትብብር እየጎለበተ መምጣቱን መረጃዎች ያመለክታሉ።

የቼክ ሪፐብሊክ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ራዴክ ሩበሽ ለኢዜአ እንዳሉትም፤ የኢትዮ-ቸክ ሪፐብሊክ ታሪካዊ ግንኙነት በበርካታ ዘርፎች ዕድገት እያስመዘገበ መጥቷል።

ለአብነትም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና የቼክ አቻቸው ፔትር ፊያላ ይፋዊ የእርስ በዕርስ የሥራ ጉብኝትም የሀገራቱን ታሪካዊ ወዳጅነት የበለጠ በማደስ ጠንካራ መሰረት መጣሉን አስታውሰዋል።

በቼክ ሪፐብሊክ ፕራግ ከተማ እ.አ.አ በ2023 የተካሄደው ታላቅ የኢትዮጵያ የጥበብና ባህል አውደ-ርዕይም የሀገራቱን የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት በማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበተርከቱን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ አስቻይ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳርም የቼክ ሪፐብሊክ አልሚ ባለሃብቶችን ቀልብ እየሳበ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

በተለይም በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የተወሰዱ እርምጃዎች የቼክ ባለሃብትች የኢትዮጵያን የንግድና ኢንቨስትመንት አማራጮች የሚያጤኑበት ዕድል መፍጠሩን አስረድተዋል።

ይህም የቼክ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ የንግድና ኢንቨስትመንት አማራጭቾ በስፋት ለመሰማራት ከፍተኛ ፍላጎት ማሳደሩን አንስተዋል።

የኢትዮ-ቼክ የኢኮኖሚ ስምምነቶችን በሚገባ በመተግበር የሀገራቱን የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር ለማበረታታት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አብራርተዋል።

ለዚህም የሀገራቱን የንግድና ኢንቨስትመንት ማህበረሰብ የሚያገናኝ የጋራ የኢኮኖሚ ኮሚሽን ለማቋቋም እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

የጋራ የኢኮኖሚ ኮሚሽኑም በሀገራቱ መካከል የእርስ በዕርስ የንግድና ኢንቨስትመንት ትስስርን ለሚፈልጉ ኩባንያዎች ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ተናግረዋል።

የኢትዮጵያን የንግድና ኢንቨስትመንት ዕድሎች በመዳሰስ የቼክ ባለሃብቶች ሊሰማሩባቸው የሚችሉ መስኮች ተለይተው እየተሰራባቸው መሆኑንም አረጋግጠዋል።

በተጨማሪም በቱሪዝም፣ መስኖ፣ ቆሻሻ አወጋገድ፣ በውሃና ንፅህና አጠባበቅ መሠረተ ልማት ዘርፎች በትብብር ለመስራት ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል።

#Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም