ቀጥታ፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ህብረት የሰው ሰራሽ አስተውሎት እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ ሆነው መሾማቸው ኢትዮጵያ በዘርፉ ላሳየችው እመርታ ተግባራዊ ምላሽ ነው

አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ህብረት የሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው መሾማቸው ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂው ዘርፍ ላስመዘገበቻቸው እመርታዊ ውጤቶች ተግባራዊ ምላሽ ነው ሲሉ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወ/ሮ እፀገነት መንግሥቱ ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ኅብረት የሰው ሠራሽ አስተውሎት (AI) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው ተሹመዋል።

ሹመቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘርፉ ላሳዩት አመራርና ኢትዮጵያ በአህጉሪቷ የሰው ሰራሽ አስተውሎትንና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስፋፋት እየተገበረች ላለው የላቀ ሚና የተሰጠ እውቅና መሆኑ ተገልጿል።

የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ሹመቱ ኢትዮጵያ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂን ሥነ ምግባራዊ መርሆች በተከተለ መልኩ በማልማት፣በመመራመር እንዲሁም ተግባራዊ በማድረግ በኩል ከአፍሪካ ቀዳሚዋ ሀገር እንድትሆን ለተሰሩ ስራዎች እዉቅና የሰጠ ነው በሚል ገልጾታል።

ይህም አህጉራዊ ትብብር የሚፈጠርበት ብሎም ለዘርፉ ተጨማሪ ሀይል እንደሚሆን ኢንስቲትዮቱ አስታውቋል።


 

በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግ እና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እጸገነት መንግስቱ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሹመት እጅግ የሚያስደስትና ለበለጠ ስራ የሚያነሳሳ ነው ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ ትላንትን መርምራ፣ የዛሬን ተጨባጭ ሁኔታ ተረድታና ነገን በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) እውቀት ላይ ተመስርታ ለመተንበይ የጀመረችው ሰፊ ስራ እውቅናን በማስገኘት ላይ እንዳለ አስታውቀዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተሰጣቸው ሹመት የመንግሥት የፈጠራ ተነሳሽነት እና የቴክኖሎጂ ቁርጠኝነት ውጤት መሆኑን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ከተመሰረተ አጭር ጊዜ ቢሆነውም ያስመዘገበው ውጤት ግን ለዛሬው ሽልማት ያበቃ የድካም ፍሬ መሆኑን አመልክተዋል።

ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ በአፍሪካ ቀዳሚ ተጠቃሽ ሀገር እንድትሆን የሚያደርጋትን በርካታ ተግባራዊ እንቅስቃሴዎችን እያከናወነች እንደምትገኝ ተናግረዋል።

ኢንስቲትዩቱ የሚፈልቁ በርካታ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ተቋማት እንደ የባህሪያቸው ወስደው ተግባር ላይ ሊያውሉት ይገባል ብለዋል፡፡


 

በአሁኑ ወቅት በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታገዙ ስራዎችን በመጠቀም ውጤት እያሳዩ የሚገኙ ተቋማት እንዳሉ ተናግረዋል።

በፍርድ ቤቶች የጉዳዮችን ፍሰት በማሳለጥና ቅልጥፍናን በማምጣት ረገድ የሰው ሰራሽ አስተውሎት እየተጫወተ ያለውን ከፍተኛ ሚና ለአብነት አንስተዋል፡፡

የሀገርን ደህንነትና ሰላምን ለማረጋገጥ ቴክኖሎጂው ሰፊ ፋይዳ እያበረከተ እንደሚገኝም ጨምረው አስታውቀዋል።

ኢትዮጵያ ያገኘችው እውቅና ለበለጠ ስራ መነሳሳትን የሚፈጥር መሆኑን የተናገሩት የቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢዋ፤በቀጣይም አዳዲስ የፈጠራ ስራዎችን በመጨመር ጉዞው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።

#Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም