ቀጥታ፡

ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ በግልጽ ራዕይና ቁርጠኝነት ባስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካ አርዓያ ሆናለች

አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎት በግልጽ ራዕይ፣ በሥነ-ምግባራዊ መርሆች በመመስረት በማልማት፣በመመራመርና በተግባር በማዋል ባስመዘገበችው ስኬት በዘርፉ የአፍሪካ መሪ እንድትሆን ተመርጣለች።

በዚሁ መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ሕብረት የሰው ሰራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው መሾማቸው ዛሬ ይፋ ተደርጓል።

ሹመቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘርፉ ላሳዩት አመራርና ኢትዮጵያ በአህጉሪቷ የሰው ሰራሽ አስተውሎትንና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስፋፋት እየተገበረች ላለው የላቀ ሚና የተሰጠ እውቅና መሆኑ ተገልጿል።

የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ሹመቱ ኢትዮጵያ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂን ሥነ ምግባራዊ መርሆች በተከተለ መልኩ በማልማት፣ በመመራመር እንዲሁም ተግባራዊ በማድረግ በኩል ከአፍሪካ ቀዳሚዋ ሀገር እንድትሆን ለተሰሩ ስራዎች እዉቅና የሰጠ ነው በሚል ገልጾታል።

ይህም አህጉራዊ ትብብር የሚፈጠርበት ብሎም ለዘርፉ ተጨማሪ ሀይል እንደሚሆን ኢንስቲትዮቱ አስታውቋል።

በሌላ በኩል ኢንስቲትዩቱ ከኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ጋር በመተባበር ያዘጋጀው "የአካባቢ ብክለት ዲጂታል ሪፖርት ማድረጊያ ሥርዓት" ዛሬ በይፋ ሥራ ጀምሯል።

ይህ አዲስ የለማ መተግበሪያ የአካባቢ ጥበቃና የብክለት ቁጥጥር ሥራን በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታገዘ የዳታ ትንተና በማከናወን ለማዘመን እንዳለመ ተጠቁሟል።


 

የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር ኢ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ተቋሙ ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ "ኤ.አይ ለሁሉም" በሚል መርህ ሀገራዊ የልማት ግቦችን የሚደግፉ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን እያመረተ ይገኛል።

ይህ መተግበሪያ ህብረተሰቡ የብክለት ጥቆማዎችን በቀላሉ እንዲያደርስና በፈጣን የዳታ ትንተና አማካኝነት ተገቢው ምላሽ እንዲሰጥ የሚያስችል መሆኑንም አስረድተዋል።


 

የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ በረከት ፍስሃጽዮን በበኩላቸው፤ መንግሥት የአሁኑንና የቀጣዩን ትውልድ ተጠቃሚነት ታሳቢ ባደረገ የኢኮኖሚ ልማት ላይ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

አሁን የለማው መተግበሪያ መንግሥት በዘርፉ የሚወስዳቸውን የፖሊሲ ማሻሻያዎችና ፈጣን ምላሾች በዳታ ላይ የተመሠረተ እንዲሆኑ ለማድረግ እንደ ትልቅ ግብዓት የሚያገለግል መሆኑን ጠቅሰዋል።


 

የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ሥርዓቱ በተለይ በከተሞች የተገነቡ የኮሪደር ልማት፣ የወንዝ ዳርቻ እና የጽዳት ሥራዎችን በዘላቂነት ለመጠበቅ ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል።

ቴክኖሎጂው ተቋማቸው በመረጃ ላይ የተመሰረተ ውሳኔ እንዲያሳልፍና የብክለት ምንጮችን በቅርበት ለመቆጣጠር እንዲቻል አቅም ይፈጥራል ሲሉ ጠቁመዋል።

"ፅዱ ኢትዮጵያን" እውን ለማድረግ ህብረተሰቡ በመተግበሪያው በኩል ጥቆማዎችን በመስጠት ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።

ይህ የዲጂታል ሪፖርት ማድረጊያ ሥርዓት መተግበር ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራና በከተሞች ውበት ረገድ የጀመረቻቸውን ስኬታማ ሥራዎች በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማስደገፍ፣ የተሻለ የአየር ንብረት ለመፍጠር ለሚደረገው ጉዞ ትልቅ አበርክቶ እንደሚኖረው ተገልጿል።

#Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #AIForAfrica

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም