ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተሰጠው ኃላፊነት ኢትዮጵያ በኤአይ ዘርፍ በአፍሪካ የያዘችውን መሪነት በጉልህ ያሳየ ነው-የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት - ኢዜአ አማርኛ
ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተሰጠው ኃላፊነት ኢትዮጵያ በኤአይ ዘርፍ በአፍሪካ የያዘችውን መሪነት በጉልህ ያሳየ ነው-የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦የአፍሪካ ኅብረት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሰው ሠራሽ አስተውሎት እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ አድርጎ መሾሙ ኢትዮጵያ በኤአይ ዘርፍ በአፍሪካ የያዘችውን መሪነት በጉልህ ያሳየ መሆኑን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት አስታወቀ።
የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት፥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ኅብረት የሰው ሠራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው በአፍሪካ ኅብረት ጉባኤ በመሾማቸው የተሰማውን ደስታ ገልጿል።
የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የተሰጠው ኃላፊነት ኢትዮጵያን በኤአይ ዘርፍ በአፍሪካ የያዘችውን መሪነት በጉልህ ያሳየ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ሹመቱ የተሰጠው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በዘርፉ ላሳዩት አመራር እና ኢትዮጵያ በአህጉሩ የሰው ሰራሽ አስተውሎትንና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስፋፋት እየተገበረች የምትገኘውን የላቀ ሚና እውቅና የሰጠ መሆኑን አመልክቷል።
ባለፉት ጥቂት ዓመታት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አመራር፣ኢትዮጵያ በዲጂታላይዜሽን እና በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፎች ያስመዘገበችው እድገት ከፍተኛ አፈጻጸም አሳይታለች።
የዲጂታል መሰረተ ልማትን ማስፋፋት፣ የኢ-መንግሥት አገልግሎቶችን ሥራ ላይ ማዋል፣ በፈጠራ ሥነ-ምህዳር ላይ መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ፣ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ኢንስቲትዩትን ማቋቋም እንዲሁም ሀገራዊ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ስትራቴጂ መንደፍ ለለውጡ ጠንካራ መሰረት የጣሉ ተግባራት መሆናቸውንም አክሏል።
በተጨማሪም ራሱን የቻለ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዩኒቨርሲቲ ለማቋቋም የታቀደው ዕቅድ፤ ምርምርን፣ የክህሎት ልማትንና አህጉራዊ ትብብርን ይበልጥ እንደሚያጠናክር የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት መግለጹ ይታወሳል።