ቀጥታ፡

በምስራቅ ጎጃም ዞን በፍራፍሬ ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ ሆነዋል

ደብረ ማርቆስ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ባላቸው ፍራፍሬዎች ልማት ሥራ ላይ የተሰማሩ አርሶ አደሮች ተጨማሪ ገቢ በማግኘት ተጠቃሚ መሆናቸውን ገለጹ።

በዞኑ ከ20 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ መሬት በቆላና ደጋ የፍራፍሬ ተክሎች እየለማ መሆኑም ተመላክቷል።

በምስራቅ ጎጃም ዞን የስናን ወረዳ አርሶ አደር ጌታሁን መንግስቴ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ከሰብል ልማት ሥራቸው ጎን ለጎን ከስምንት ዓመት በፊት በትንሽ መሬት ላይ የጀመሩት የአፕል ልማት ሥራቸው ተጠቃሚ እያደረጋቸው ነው።

በአሁኑ ወቅት ከሩብ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ልማቱን እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።


 

በየዓመቱ ከሚሰበስቡት የአፕል ምርት እስከ 30 ሺህ ብር ተጨማሪ ገቢ እያገኙ እንደሆነና ቆጥበው ተጨማሪ ሃብት ለማፍራት እንዳገዛቸው ተናግረዋል።

ዘንድሮም የአፕል ምርት አያያዙ የተሻለ መሆኑን ገልጸው፣ በምርት ሽያጩ ካለፈው ዓመት የተሻለ ገቢ ለማግኘት ተግተው እየሰሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል።

በዞኑ የጎዛምን ወረዳ ነዋሪው አርሶ አደር የሻነህ ጓዴ በበኩላቸው እንዳሉት ከአቮካዶ፣ ማንጎ እና ሎሚ ምርት ሽያጭ በዓመት ከ50 ሺህ ብር በላይ ገቢ እያገኙ ይገኛሉ።

ከሰብል ልማት ሥራቸው ጎን ለጎን እያካሄዱት ያለው የፍራፍሬ ልማት ገቢያቸውን ከማሳደጉ ባሻገር ልጆቻቸውን የተመጣጠነ ምግብ ለመመገብና ጤናማ ሆነው እንዲያድጉ እያገዛቸው መሆኑን አስረድተዋል።


 

በምስራቅ ጎጃም ዞን ግብርና መምሪያ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ባለሙያ ተሾመ በላይ፣ በዞኑ ከ20 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የፍራፍሬ ልማት እየተከናወነና በልማቱም አርሶ አደሮች በመሳተፍ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።

ዘንድሮ በዞኑ ከለማው አቮካዶ፣ ማንጎ፣ ብርቱካን፣ ሎሚ፣ ፓፓያ፣ አፕልና ሌሎች የቆላና የደጋ ፍራፍሬዎች እስካሁን ከ80ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ተሰብስቦ ለገበያ መቅረቡን ጠቁመው፣ በቀሪ ወራትም የበለጠ ምርት ይቀርባል ብለዋል።

ከፍራፍሬ ልማት የሚገኘውን ጥቅም ለማሳደግ በመጪው የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የሚተከሉ ከ818 ሺህ በላይ የፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸውንም ተናግረዋል።

ባለፈው ዓመት በዞኑ ከፍራፍሬ ልማት ከ278ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለገበያ መቅረቡን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም